Samstag, 28. Februar 2015

ከትብታቡ ባህል ያልተላቀቀ ወያኔን መክሰስ አይችልም



ብዙ ግዜ ምንም ነገር ውስጥ ታግ እንዳታደርጉኝ  ብዬ ጠይቄ ነበር፡፡ ግን ብዙ ሰዎች ከልጅነት ጨዋታ ገና ያልወጡ በመሆናቸው አልያም  በውስጣቸው ያበበው የአምባገነንነት ስሜት ሊሰሙኝ አልቻሉም፡፡ እኔ ባዩሽ አበበ የማንም የፖለቲካ አባል ደጋፊም ተቃዋሚም አይደለሁም፡፡ በግሌ ያቀረብኩት አስተያየት ሁሉ ምንአልባት አንደዬ አንዱን ሌላ ግዜ ሌላውን ይነካ ይችላል፡፡ ይህ ማለት እኔ ያንንም ይህንንም አይደለሁም፡፡ ለመሆንም በጭራሽ ፍላጎት የለኝም፡፡ ኢትዮጲያ ውስጥ እንዳየሁት እና እንደተረዳሁት፤ የመንግስት ስራ አስፈጻሚ ብቻ ሳይሆን በህብረተሰብ ውስጥ ሙስና ያለእና የሚኖር ሊጠፋም የማይችል መሆኑን ተገንዝቤአለሁ፡፡ ምንም እንኩዋን ወያኔ ኢሕአዴግ 23 ዓመት በስልጣን ቢቆይም፤ ብቻውን ግን ሙስናን ከሕብረተሰቡ ውሥጥ አጠፋለሁ ማለት የማይቻል ሀቅ መሆኑንም ተገንዝቤአለሁ፡፡ በሌላ መልኩ ተቃዋሚም ቢመጣ እና ስልጣን ቢይዝ ይህንን ልቅ የሄደ የኖረ ሙስና ባህሪ ያስተካክላል ብዬ አላምንም፡፡ ይህንም ያደረገው እርስ በእርሳቸው የፖለቲከኞች መናናቅ እና ሁሉም እንዳገኘ በሚያደርገው የፕሮፖጋንዳ ወሬያቸው ነው፡፡ እንደእውነቱ ሙስና የመታው አገር ውስጥ፤  ለሴት ምንያህል አስቸጋሪ መሆኑን በእራሴ ሕይወት ተረድቻለሁ፡፡ ሙስና የመንግስት አካል የሆነ ስለፈለገው ብቻ ሳይሆን ፤ ከቁጥጥር ውጭ በሆነ የህብረተሰብ ባህሪ፤ ፈሪሀ እግዚአብሄር ማጣት  እና ግድየለሽነት፤ የንዋይ ፍላጎት ማደግ ተጠያቂ ሊያደርገው ይገባል፡፡ ይህ ማለት ማንም የህብረተሰብ አካል ከቻለ ብዙ ነገሮችን በሙስና አጣሞ እራሱ ብቻ ተጠቃሚ የሚሆንበትን እና በማተርያል የሚያድግበትን ዘዴ ፈላጊ ሆኖአል፡፡

ልናየው የሚገባ

ለምሳሌ እኔ አንድ ወጣት ልጅ ቀበሌው ሊቀመንበር ጋር በመመሳጠር ለ9 አመት ያህል በራፌን ለጋራጅነት በመውሰድ ስራ እንዳልሰራ እንዳጣ እና እንድከስር ፤ ንብረት ይዠ እምበላው እስካጣ አድርገውኛል፡፡ ይህንንም የአካባቢው ህብረተሰብ በሙሉ እያወቀ ሳለቅስ እና ስሰቃይ ልጆቼን ስበትን ዝም ብሎ ሕብረተሰቡ የምለከት ነበር፡፡ ጭራሽ አበደች እያለ ከልጁ እና ከቀበሌው ስራ አስፈጻሚዎች ጋር በማበር ይሰድቡኝ ይዘልፉኝ ነበር፡፡ ስለዚህ ሙስናን የሚያቆመው ሕብረተሰብ እንጂ ፖሊስ ወይም ዳኛ ሊሆን አይገባውም፡፡ ብዙ የኢትዮጲያ ሙስና የሚካሄደው ግልጥ ባልሆነ መንገድ ነው፡፡ ለዚህ ህብረተሰባችን በቂ ለምድ አካብቶአል፡፡ የሚደብቅለት እራሱ ነውእና፡፡ ወይ እሱ ጥሩ ሰው፤ እሱዋ እየተባለ፡፤ የበላ መጋበዝ ያቅበታል፡፡ አንተ የፈራሃውን በረከት ከቤተመንግስት ወጥቶ እንዲያባርርልህ ትፈልጋለህ፡፡  ነውርን ነውር ለማለት የሚደፍር ባህሪ የለውም፡፡ ነውር የሚሰሩ ሰዎችን ህብረተሰቡ ሲተባበር ነበር የተመለከትኩት፡፡

 ሕብረተሰቡ ከቀናው ሰው ጋር አብሮ የመጉዋዝ ባህሪ፤ ከየትም ያምጣው አንቱ ከተባለ አንቱ ነው፤ ሁሉም ሰጋጅ ነው፡፡ ህብረተሰቡ የጋራ ጥቅም የሆነው የባህሪ ለውጥ ለማሳየት የተቸገረ ነው፡፡ ሐብረተሰቡ  እንደሌላው አካባቢ እርስ በእርሱ የመጠባበቅ ባህሪ ፤ መንግስትን እንደእራስ የማየት ባህሪ በጭራሽ ኖሮት አያውቅም፡፡  ወያኔ ኢሕአዴግ ባይፈልገውም ይህንን ባህሪ ግን በጭራሽ ሊያስቆም አይችልም፡፡ እንዴት ይህ አስቸጋሪ የሆነ ስልጣን አምሮት፤ እንደውነቱ በስልጣን መቆየት እንደፈለገ ነገሩ እኔን ያስቀኛል፡፡ እኔ በስልጣን ብሆን አንድ ቀንም ኢትዮጲያ ውስጥ ባለስልጣን ለመሆን ፍላጎት የለኝም፡፡ የዚህም ምክናያት ከጥንት ጀምሮ ህብረተሰቡ ለኢትዮጲያ መንግስት የባህሪ ተባባሪነት አልገነባም፡፡ ይህ የመንግስቱሀይለማርያም ችግርም ነበር፡፡ „ ቂጡን በሳንጃ“ ብለዋል፡፡ ሰውየው ከሄዱ በሁዋላ ደግሞ በመጡ ይላል፡፡ አይገባኝም፡፡

 ኢትዮጲያን ማስተዳደር በጣም ከባድ እና አስቸጋሪ ነው፡፡ ማንም ከቻለ ሙስናን ይፈልጋል፡፡ በቃ እራሱ በይፋ ሙስና የገቡትን ሰዎች ቤት እየሄደ ድግሱን ይበላል ይጠጣል፡፡ ይህን ፈረንጅ አያደርገውም፡፡ እንግዲሕ የእያንዳንዱን ባለስልጣን ፎቶ በየቤታችን ለጠፈን ያስፈራሩልን እንደሁ አላውቅም፡፡ ነገም ዶ/ር ብርሃኑ ቢመጣ ያው ነው፡፡ በቃ ሕብረተሰቡ መንግስትን በባህሪ ለውጥ መደገፍ አይፈልግም፡፡ አማላጅ እና አንገት ማቅለስለስ፤ ፍርድ እና በማያገባው ገብቶ አድማ ይህ የአድርባይነት ስሜት የገነባ ነው፡፡ መጀመሪያ ሰው ከዚህ አዘቅት ውስጥ መውጣት አለበት፡፡

ሌላው

ልምሳሌ እኔን ታግ አታድርጉኝ፤ በጭራሽ ከምትሉት ነገር ጋር ግንኙነት የለኝምም ብዬ ታግ የሚያደርጉኝን በግልም በሚዲያም ባስተላልፍ ይህንን ቀጥለውበታል፡፡ ይህ ማስረጃነቱ ደግሞ ምንያህል በሕብረተሰቡ ውስጥ አምባገነንነት ሰርጦ እንደገባ የሚያስረዳ ነው፡፡ የግድ እንደእኔ አስቢ የሚለኝ ሰው አልፈልግም፡፡ ለእኔ ማንም ማንም የሚጠቅመኝ የለም፡፡ ሊጠቅመኝ የሚችለው፤ ሶስት ቀንም ቢሆን ስርአት ያለው አገር ማየት ነበር፡፡ ይህ ግን ዘወትር ባለጡንቻ የሚኖርበት አገር እሰየው በማለት ፖለቲከኞች ሁሉ ገዢውም ተቃዋሚውም ኢትዮጲያን ትናንት ገነት ነበረች አልያም ዛሬ እየተባበሉ መሙዋገት ሆኖአል፡፡ ለእኔ እይታ የኤትዮጲያ ገነትነት ጡንቻ ላለው፤ ገንዘብ መክፈል ለሚችል እና ነገርን በጉቦ አጣሞ ማስፈጸም ለሚችል ክፉ እና ደፋር ሰው ነው፡፡ ይህን አይነት ሰው እያደር የሚብስበት እንጂ የመጣ ቢመጣ ሊለውጠው የሚችል የለም፡፡ 23 አመት ሙሉ ወያኔ ላይወድቅ ነገር እርብርቦሽ ከማድረግ፤ 23 ዓመት ሙሉ የባህሪ ለውጥ ላይ የሰው ልጅ አተኩሮ በነበር፤ ኢትዮጲያ በተለወጠች ነበር፡፡

ግን ይህንን ባለጌ ባህሪ ለመለወጥ ቀርቶ ፤ ብልግና በውስጣችን  አለ እንኩዋን ብሎ ደፍሮ ሊናገር የሚችል አልተፈጠረም፡፡ ስለዚህ እኛ ማለት በክርስቶስ ስም የምናገረው ነውርን ጎጆ አድርገን በውስጡ  የምንኖር እንመስላላን፡፡ ትግሬ ወያኔ ወያኔ ቢል ለኪሱ ነው እንጂ ለወያኔ የሰሩለት ምንም ነገር ይኖራል ብዬ አልገምትም፡፡ ሌሎችም የወያኔ ፓርቲዎች ሁሉ እንደአብዛኛው ሕብረተሰብ ለኪሱ ነው፡፡ በቃ ሁሉም አንድን ገሎ መሸጋገር ብቻ ነው፡፡ ይህ ወያኔ ያመጣው ነው ብለን ደምድመናል፡፡ ስለዚህ ተቀብለነዋል፡፡ ግን ዛሬ ደፍሬ ልናገር፤ ይህ ወያኔ ሳይሆን ባህሪያችን ያመጣው ነው፡፡ ማንኛውም መንግስት የተባለ አካል አገር ቢረጋጋለት የሚደሰት ይመስለኛል፡፡ ግን ካለአጋዥ ማንም የትም አይደርስም፡፡ 23 አመትም በእርግጥም ብዙ ነው ፡፡  በዚህ ባህሪ ስራ መስራትም አልችልም ብሎ ወያኔ ቢደመድም እና ቢለቅ ከዛ በሁዋላ ያለውን ጉድ እናይ ነበር፡፡
ውሸት አፍንጫ ሲሞላ ያስነጥሳል እንዴ ? ብዬ ስገምተው፤ ስለኢትዮጲያ የሚባል ነገር ሳስበው ብዙ ነገር ያበቃልን በገዛ እጃችን እራሳችንን ለውንብድና ተግባር አሳልፈን የሰጠን ነን ብዬ እገምታለሁ፡፡ እራሱ እኔ በእራሴ የተገፋሁት ግፍ በህብረተሰቡ ውስጥ ውነት እውነት አለችእን ብዬ መገመት አላዳገተኝም፡፡

 አንድ ነገር አለ፤ ሁሉንም  የመንግስት ሰራተኛ መናቅ እና ገደል መክተት ጥሩ አይደለም፡፡ ግን አንድ ነገርነ አለ፤ እነዚህን ጥሩ የሚሰሩ ግን ለመደገፍ እንኩዋን 23 አመት ሙሉ አልቻልንም ነበር፡፡ ምክናያቱም፤ ወያኔ መውረድ አለበት ተብሎ ስለተገመተ፡፡ ወያኔም አልወረደ ሕብረተሰቡም ውስጥ መጥፎ ባህሪ እየሰረጠ ሄደ፡፡ በቃ የሰረቀን ሰው አዳናቂ፤ ጠበል አጣጭ ድግስ በይ የሆነ ሕብረተሰብ መካከል፡፡ እንኩዋን ወያኔ ተቃዋሚም ቢጨመር ማስተካከል አይቻልም፡፡ ማንም ኢትዮጲያን ማስተካከል አይችልም፡፡ ፈሪሃ እግዚአብሄር በምድሩ እንዲጠፋ ዘመኑ የንዋይ ሆኖአል እና፡፡ ለዚህ ነው „አይታ የማታውቀውን የሰው ጃኖ ለብሳ ፤ ነይ ተመለሽ ቢሉዋት ወዴት ተመልሳ „ያልኩት፡፡ ስለዚህ እኔን ታግ አታድርጉኝ፤ በብዙ ሰዎች ባህሪ ኢትዮጲያን ወዴት አቅጣጫ እየሄደች እንዳለች አውቃለሁ እና፡፡ ግን አንድ ነገር አለ፡፡ አንድም ተቃዋሚ ውጭ መትረፍ የለበትም፤ ምክናያቱም፤ ተቃዋሚ የለም ማለት በአገር ውስጥ መደነጋገር ይኖራል እና፡፡ ይህ ገዢ ፓርቲውን አይጠቅመውም፡፡ ሕብረተሰቡ ግን የለመደው ባህሪ ነው፡፡ የቻለ ዘዴ እየፈለገ ይኖራል ያልቻለ ያለቅሳል፡፡ ውሸት በውሸት፡፡ ሁሉ ነገር ውሸት፡፡ እግዚአብሄር ሆይ አንተስ ምን ትላለህ? „ የልባችሁን መሻት መርምሩ“  ባዩሽ

እፈረሰ አገር ምን ፓርቲ ያስፈልጋል፤ ወንበዴ እንጂ

እፈረሰ አገር ምን ፓርቲ ያስፈልጋል፤ ወንበዴ እንጂ

የኢትዮጲያ ህዝብ ለመንግስቴ/ለገዢ ፓርቲ/ ሲል፤ እንጂ ለአገሬ የሚል የለም፡፡ ይህን ባህሪ መገንባት  አልቻልንም፡፡ ሚኒሊክን ፣ ሐይለስላሴን  ደግሞም ደርግን፤ ኢሰፓ ኢሰፓ ሲል፤ አሁን ደግሞ አፍቃሪ ኢህአዴግ ወያኔ ወያኔ ይላል፡፡  ደግሞም ነገ   ግንቦት 7 ይምጣ አልያም ሌላ ሲል ለእሱ ሲያጫፍር ይገኛል፡፡ አበላሉን የሚያውቅ ዘዴኛ ህብረተሰብ ፖለቲከኞቻችንን ማፍራታቸውን አላወቁም፡፡  እስኪ በፈጠራችሁ አገሬ የሚል  እንጂ ፓርቲ ነጥሎ የማያፈቅር መሪ ፍጠርልን ብላችሁ ጸልዩ፡፡ ሽ ዘመን ይኖር ይመሰል፤ ሌባውን ሁሉ በጉያህ ሸጉጠህ፤ ሴት አስለቃሹን ደሃ አሳዳጁን በብብትህ ይዘህ የእኔ ልጅ ወርቅ ነው የምትል ሁሉ እስኪ አሰብ አድርግ፡፡ የጋራ ነገር የሚፈጥር ሕዝብ ከየት እንፍጠር፡፡ ይህን ፓርቲ አፍቃሪ ህዝብ ይለወጥ ብላችሁ ጸልዩ፡፡ ይህ ካልሆነ፤ ሁሉም የእራሴ የሚለውን የተነከረበትን ባህር ዋኝቶ መውጣት አይችልም፡፡


እስኪ ስንቱ ነው አገሬ ወገኔ የሚል፡፡ ሁልግዜ ፓርቲ አፍቃሪ፤ መሪ አፍቃሪ፤ ሚኒሊክ ፣መለስ ስትል መዳከር ብቻ፡፡ አገሬ በል የኢትዮጲያ ሕዝብ፣ ሰላሜ በል የኢትዮጲያ ህዝብ ፣ወገኔ በል የኢትዮጲያ ህዝብ  ፣ነጻነቴ በል የኢትዮጲያ ህዝብ፣ ድህነቴ ጥማቴ በል የኢትዮጲያ ህዝብ፡፡ መብቴ በል የኢትዮጲያ ህዝብ፤ ፓርቲዬ እያላችሁ ከአጽም ጋር አትታገሉ፡፡ ሚኒሊክም መለስም አልፈዋል፡፡ እኛ መኖር ነው የምንፈልገው፡፡ እያለቀሱ መብት ተጉዋድሎበት ፍርድ ተዛንፎበት መኖር ይብቃን በሉ፡፡ ያም ያም እየተነሳ አይገልምጠኝ በሉ፡፡ አንተ ሌባውን በጉያህ የደበክ፤ መጀመሪያ ከቤትህ ያለውን አስወጣ፡፡ አንተ ፍርድ የምታጉዋድል፤ መጀመሪያ እራስህን ለውጥ፡፡ በቃ ፓርቲ አፍቃሪ ሳይሆን አገር አፍቃሪ በእግዚአብሄር ስም ሁኑ፡፡

 ምንም ቢሆን አንድ ዘር ከአንዱ ዘር በልጦ ለመኖር ይቸገራል እና፤ አንተ እበልጣለሁ የምትል ውል ስራ፡፡ እንዴት እንደምትበልጥ የምታሳውቀው፤ እራስህን ነጥለህ በማዳን ሳይሆን ሌላውንም ፤ሰው ነው ወገኔ ነው ስትል ነው፡፡ ካልሆነ መብለጥ እንዲህ፤ ከማን ጋር ተወዳደርክ እና፡፡ ዘር ከዘር አይወዳደርም፡፡ የዘራው አንድ እግዚአብሄር ነውእና፤ መርገምትህን አትከናነብ፡፡ ይገርመኛል ይደንቀኛል፡፡ ሌባ ጋር እየበላ እያቦካ እየደገሰ ጣትን ቤተመንግስት ላይ መቀሰር፡፡ ስንቶቻችን ነን ያንን የምናደርግ? ለዘመናት የሚጫወትብንን አድርባይነት እንዴት እንላቀቀው?አንተ ፓርቲ አፍቃሪ የሆነክ፤ ሌላውም የእራሱ የሚያፈቅረው ፓርቲ እንዳለ ለምን ዘነጋህ፡፡ ጆሮ ያለው ካለ ይስማ፡፡ ኢትዮጲያ የደከማት አገር ሆናለች እና መደገፍ እንጂ መገፍተር አያስፈልጋትም፡፡ በቁዋፍ ያለችውን አገርህን ለመታደግ፤ ወያኔም ሁን ሌላ ፓርቲ አፍቃሪ መሆንህን ወደጎን ተወት አድርግ እና አገር አፍቃሪ ሁን፡፡ ፓርቲህ የሚኖረው አገር ሲኖር ነው፡፡ እፈረሰ አገር ምን ፓርቲ ያስፈልጋል፤ ወንበዴ እንጂ፡፡
ባዩሽ

Mittwoch, 25. Februar 2015

ከከሳሽነት ወጥተን ወደእርምጃ እንሸጋገር



               ለዚህ ጽሁፌ መነሻ ያደረኩት „በአሰሪዎቾ የታገተችው ኢትዮጵያዊት የሰቆቃ ደምጽ“ !    የሚለውን የተለቀቀ አርቲክል ካነበብኩ በሁዋላ ነው፡፡ ይህንንም በፌስ ቡክ ድረገጼ አካፍያችሁዋለሁ፡፡ ማንበብ ትችላላችሁ፡፡ ሳነበው ነገሩ ውስጤን የመናደድም ሆነ የቁጭት ነገር ሲቀሰቅሰው ይሰማኛል፡፤ የዚህ አይነት ስሜት ውስጤን ሲረብሸው መጻፍ እመርጣለሁ፡፡ ልተኩስስ ብል የትኛው አካል ላይ በምንስ መሳሪያ፡፡ ብእርን የመረጥኩትም ለዚህ ነው፡፡ ብእርም ጥይት መስሎ ሌላ የሚደግንብህ እንደሚከፍት አውቃለሁ፡፡ ቢሆንም፤ ትእግስተኛው ነጭ ልሙጥ ወረቀት የማይቀበለው ነገር የለም እና የስሜቴ እና የቁጭቴ ተካፋይ ጉዋደኛ አድርጌዋለሁ፡፡ በአረብ አገር ታገተች የተባለችው ልጅ ብዙ ነገር እንዳይ አድርጎኛል፡፡ ሊረዳት የፈለገው አካልም ስሞታ በማሰማት ይመስላል፡፡ ግን ሰሚ በለለበት አለም ዋይታ ለምኑ ፡፡

                ይህንን ዜና ያስተላለፉት ልጆች ያለችበትን ካወቁ፤ ለምን ወደ ሰብአዊ ድርጅቶች አይሄዱም እና አይጠይቁላትም፡፡ የዚች ልጅ ዜና እንዲህ በይፋ ከታወቀ፤ ሴቶችንም ሊረዳ የሚችል የሆነ የግልም ድርጅት ቢሆን  በአረብ አገር አካባቢ ላይጠፋ ይችላል ብዬ እገምታለሁ፡፡ በዚህ ህገውጥ የሆነ የሰው ባርነት በየአለማቱ የቆሙ ሰዎች ይኖራሉ፡፡ በአረብ አገርም ሁሉም ሰው አንድ አይነት የሆነ አረመኔአዊ ተግባር የሚያካሂድ አይደለም፡፡ በእርግጥ የቤት ሰራተኛ ጉልበት ብዝበዛ በአገራችንም ቢሆን ሲታይ ኖሮአል፡፡ ዛሬም ይታያል፡፡ የሰው ልጅ ሲባል ጉልበት እማይጠቅመው ነው፡፡ ስለዚህ እኔ በበኩሌ፤ አሁን ይህን አይነት ችግር ሊረዳ የሚችል ማነው የትስ ይገኛል ብለው እዛው አካባቢ ያሉት ኢትዮጲያውያኖች የሳውዲ አረቢያን ውስጡን መበርበር እና ማግኘት አለባቸው፡፡ እራሳቸውን ለመርዳት እና ለመታደግ ዘዴ መቀየስ ይገባቸዋል፡፡ ሌላው ቢቀር ህጋዊ የሆኑት ከፖለቲካ ውጭ የሆነ ማህበር በማቁዋቁዋም ከእራሳቸውም አልፈው ሌላውን መታደግ ይችላሉ፡፡ ከፖለቲካ ውጭ ያልኩበት ምክናያት፤ ገዢውም ተቃዋሚውም ይህንን የሰውልጅ ሰቆቃ የፖለቲካ ፍጆታ አድርገው፤ በፉክክር ማህበሩ እንዳይፈርስ ለማድረግ ነው፡፡ ሁሉንም ማህበር የፖለቲካ ጣልቃ ገብነት ካለው፤ ከእንግዲህ በሁዋላ ኢትዮጲያዊ በየትም አገር ቢሄድ ከመበደል የጸዳ አይሆንም፡፡ ስለዚህ ህብረተሰቡ ወይም ማህበረሰቡ የመጀመሪያውን ደረጃ ሰብአዊነትን ለማግኘት የምገምተው፤ ከማንኛውም ፖለቲካ የጸዳ የመረዳጃ ማህበር ማቁዋቁዋም ብቻ ነው፡፡ ዛሬ ብዙውን ግዜ የተላመድነው በደልን ማውራት እንጂ ከበደል እንዴት እንደምንወጣ ዘዴ መፈለግ ተስኖናል፡፡ ኢምባሲው አይረዳም ከተባለ ደግሞ ፤በቃ አለመርዳቱን ተቀብሎ ሌላ ዘዴ መቀየስ ነው፡፡  ሽ ግዜ ይህ ቢሰማ ዋጋ ቢስ ነው፡፡ እንዳውም ሲደጋገም የፖለቲካ ፍጆታ ሆኖ ይሰለቻል፡፡ ሰለኢህአዴግ ብዙ ሰምተናል፡፡ እስኪ ደግሞ እራሳችንን ማዳመጥ እንጀመር ባይ ነኝ፡፡ የኢህአዴግ አላደረገም የምንለው ነገር የተደጋገመ ሆነ፡፡

                  ዞሮ ዞሮ የመጀመሪያው አላማ መሆን ያለበት ስብእና ነው፡፡ መቀደም ያለበት፤ እነዚህ ሴት ልጆቻችን ወይም እህቶቻችሁ ከሚደርስባቸው የቁም እስር፤ የአይምሮ ቅጣት እንዲወጡ ማድረግ ነው የሰው ልጅ ተግባር መሆን ያለበት፡፡ ከአገር ያስወጣቸው የኦኮኖሚ ችግር ነው፡፡ ኢትዮጲያ ከአለም አንደኛ በመሆን ዘወትር የምትወሳ ደሃ አገር ነች፡፡ ይህ እንግዲህ ወደፊትም ለረጅም ግዜ ይቆያል፡፡ እራሳችንን መሸንገል የለብንም፡፡ ትልቁ ስህተት እራስን መዋሸት ነው፡፡ ለማንኛውም ነገር ሕግ አስፈላጊ ነው፡፡ አሁን የማየው ነገር ፤  ፖለቲከኞቻችን   እልክ እና ፍልሚያ ደግሞም ስም መጠፋፋት እንጂ ምንም አይነት የፖለቲካ ስራ በሁሉም አይታይም፡፡ ኢህአዴግም ባለው በእራሱ መንገድ ቀጥሎአል፡፡ ተስማማችሁ ወይሰ አልተስማማችሁ በማለት ህዝብንም አያማክርም፡፡ ይህም ሁኔታው ህዝብን ተስፋ እንዲቆርጥ እና እንደአለፈው ዘመን ተቃዋሚን ተስፋ በማድረግ  አልያም በቃ እንዲህ ከሆነ የእራሴን መንገድ ልጠቀም ያለ ይመስላል፡፡ ግማሹ በሙስና ለመክበር ሲጥር፤ ያልቻለው አገር ጥሎ እግር አውጪኝ ያለ ይመስላል፡፡ ይህ ፖለቲካ የፈጠረው መደነጋገር በየአቅጣጫውም የእሮሮ ድምጽ ይሰማል፡፡ ውጭ አገር እንደሎቶሪ የሚታይበት ባህል ያካበተችው ኢትዮጲያ፤ የቸገረውም ያልቸገረውም ፍርጣጭ ሆኖአል፡፡ አንዳንዱ ለዳቦ አንዳንዱ ውጭ አገርን ለጉራ ይጠቀምበት ይራወጣል፡፡ ያም ሆነ ይህ የፖለቲከኞቻችንን የጎሪጥ መተያየት እና የብሄር የሚለው አንዱ ገንቢ ሌላው ናጂ የሆነው የፖለቲካ አካሄያድ የኢትዮጲያን አቅጣጫውን ሊያስተው     ደርሶአል፡፡ ፖለቲከኞች ወደህዝብ ሳይሆን ወደእራሳቸው የግል አላማዬ የሚሉት ገብተው ይዳክሩ ይዘዋል፡፡ ይሳካላቸው አይሳካላቸው የሚለውን እኛም መመልከት ትተነዋል፡፡ እንደለሉ አድርጎ መኖርን መርጠናል፡፡ እራሳቸውን ማስተካከል ያቃታቸው እኛን ያስተካክሉናል ብሎ ተስፋ ማድረግን ከነአካቴው ገደል አፋፍ ላይ አቁመነዋል፡፡ የዚህ አይነት መደነጋገር ደግሞ፤  በእጅጉ ሰለባ ያደረገው ሴቶችን እና በአጠቃላይ ወጣት ስደተኞችን ነው፡፡ በቃ የኢትዮጲያ ወጣት አገር እንደለለው እየተደረገ በነቂስ እግር አውጭኝ ብሎ በሕገወጥ ደላሎች የተነሳ ስቃይ እየደረሰበት ነው፡፡

                 እንደእውነቱ ከሆነ በአረብ አገር እየተሰቃዩ ነው የሚባሉት ወጣቶች ጠላታቸው የቀጠራቸው አረቡ ሳይሆን የገዛ ወገናቸው በእራስ ወዳድነቱ፤ ኪስ ለማዳለብ ወይም ደግሞ መተዳደሪያው በማድረግ በጭፍን አሳልፎ የሰጣቸው ነው፡፡ ለበረሃ እራት ለአውሬ መጨዋቻ ያደረጋቸው፡፡  የአረብ አገር ሰራተኛ ሁሉም ባይሆኑ፤ ግን በእራሳቸው እጅ የከፈሉት ጠላት፡፡ እሱን ነበር ቀድሞ መምታት፡፡ ግደሉት ማለቴ አይደለም፡፡ ደግሞ ግድያ አወጀች እንዳትሉኝ፡፡ በቃ ወደፍርድ ቤት የሚቀርብበትን መንገድ ፤የከፈላችሁት ገንዘብ እንዲመለስ ማድረግ፤ ማሳሰር ማስፈርድ ነበር፡፡ ይህ ለጅብ እንዲሰጣችሁ በገዛ እጅ የከፈላችሁት ጋር ነው ቀድሞ መታገል፡፡ ሁልግዜ ትልቁ ችግራችን አጠገባችን ያለውን ጠላት ሳንቁዋቁዋም የውጩ ላይ የምናደርገው ትችት ነው፡፡ ለምሳሌ ብንወስድ፤ መነሻችን ወያኔ ተቃዋሚን ባንዳ ይላል፡፡ ተቃዋሚ ወያኔን ባንዳ ይላል፡፡ ሁልግዜ ውድቀትን ወደላሌ ማሸጋገር የለመድነው ይመሰላል፡፡ የውጭ የምንለውን ሸክም በማሸከም ከእራሳችን ውድቀት የምንሸሽ ብዬ እገምታለሁ፡፡ በቃ የቤታችንን አመል ወደሌላ ማላከክ፡፡ ይህ ሁሉ ነገር ወንጀለኛን እንዳናይ ያደርገናል፡፡  በሰራው ወንጀል እንዲጠየቅ ለማድረግ የምናደርገው እርብርብ የለም፡፡ ይህን ለምደነዋል፡፡ በቃ ኢሌጋልነት፤ እራስን ወዳድነት ፤ እና ሙስና አስተዳደሩ ብቻውን ሊያጠፋው የሚችል ነገር ከእንግዲህ ሊሆን አይችልም፡፡

                       ይህ በጨካኝ ሰዎች የሚደረግ እርምጃ ሊያቆመው የሚችለው ሕብረተሰቡ እራሱን በሰብአዊነት፣ በማህበር በመደራጀት፣ በግልጽነት  እና እራስን በእራስ የመርዳት ባህሪ ሲገነባ ነው፡፡ ዘወትር ከሌላ ይረዳናል ብለን የምንጠብቀው መጠበቅ ሰነፍ እና አልቃሻ ምስኪን ነው የሚያደርገን፡፡ ሰው አይምሮ አለው፡፡ ስለዚህ ዘወትር ከመንግስት ወይም ከዚህ ከዚያ እያልን መጠበቃችንን ማቆም እና እኛው እራሳችን ወደእርምጃ ለመግባት መማር መላመድ አለብን፡፡ ስለዚህ አረብ አገር ያሉ ወጣቶችን ሊረዳቸው የሚችል እራሳቸውን በእራሳቸው ማደራጀት እና ችግራቸውን ወደኢምባሲው ከማሸከም በእጃቸው ማድረግ እንጂ ሌላ አማራጭ የለም፡፡ ከሌላ መጠበቅ ቆማጣ የሚያደርግ የሕይወት ልምድ ያከናንባል፡፡ ለምሳሌ ገዢው ፓርቲ ላይ ሁሉንም አገር ውስጥ ያለውን ጥፋት ማሸከም፤ ባህሪያችንን እና የአስተሳሰብ ውድቀታችንን እንዳናይ ሲያደርግ፤ ተቃዋሚንም ብቻውን ወደስልጣን ይመጣል ብሎ ማሰብ፤ ሁሉም አልሸሹም ዘወር አሉ ይሆናል፡፡
ባዩሽ

Dienstag, 24. Februar 2015

ወጣቱን ማን አቅጣጫ ያሳየው?????



ወጣቱን ማን አቅጣጫ ያሳየው?????


እናንተ ኢትዮጲያውያኖች፤ በአሁን ሰአት ከበድ ያለ ጥላቻ ከየአቅጣጫው እየጎረፈ እንደሆነ በማህበራዊ ሚዲያ የሚደረገውን የእርስ በእርስ ስድድብ እና ዝልፊያ እየተመለከትኩ ነው፡፡ እውነትም ጥላቻን ማቆም የምንችልበት ሁኔታ እንደለለ እያየሁት ነው፡፡ ይህ እንዳይሆን፤ የእምነት ቤትም እንዲሁ ውስጡ ለሁለት የተሰነጠቀ አይነት ነገር ሆኖአል፡፡ የሀይማኖት መሪዎች የፍቅር አስተማሮነትን አዲዎ ብለው የተሰናበቱ አልያም ተስፋ የቆረጡ ይመስላል፡፡ ይሁን እና አለማችን ክፉና ደጉን በመለየት፤ ሚዲያዎችን ሁሉም እንደሚፈልገው ሄዶ እንዲስተናገድ የለየች ትመስላለች፡፡ ይህን ግን እኛ ኢትዮጲያውያኖች  መለየት ያቃተን ይመስላል፡፡ ይህ እንዳይሆን የፖለቲካ አቅጣጫ የሚያሳየን አላገኘንም፡፡ እንደዘወትሩ ፖለቲከኞች እርስ በእርሳቸው አይጥና ድመት ሆነው ተፋጠዋል፡፡ ጠበንጃም እየተማዘዙ ነው፡፡


ለማለት የፈለኩት፤ ምንም እንኩዋን በሕዝብ መካከል መደነጋገር እና አቅጣጫ ማጣት ቢኖርም፤ ግን ሁሉም አፉን ዘግቶ የሚቀመጥበት ዘመንን ያለፍን ይመስላል፡፡ ሰው ስሙን እና መልኩንም ቀይሮ የሚፈልገውን የተከለከለውን አልያም በተለምዶ መናገር የፈራውን፤ እየተናገረው ይገኛል፡፡  ፌስ ቡክ ከእንግዲህ ማንም ሊያግደው የማይችል ማህበራዊ ሚዲያ ሆኖአል፡፡ ሰውም የገነባውን ፍርሃት ከልቡ ሲያወጣ ብዙዎች እንደማያደርጉት እራሱን ይገልጣል፡፡ እያንዳንዱ ለእራሱ ጋዜጠኛ የሚያደርገውእና ውስጡንም አውጥቶ የሚዘከዝክበት ሆኖአል፡፡ ይህንም አለም በሙሉ ተቀብላ ይለፍ የሰጠችው ነገር ሆኖአል፡፡ የፈለከውን እንደፈለገህ የምታስተላልፍበት ዶሞክራሲን እነሆኝ ያለ ይመስላል ፌስ ቡክ፡፡ በውነትም ይህንም ሚዲያ የማይፈልጉት አምባገነኖች በአለም ዙሪያ በአገራቸው እንዳይኖር ጥረት ቢያደርጉም፤ ማቆም የማይቻል እራሱን ነጻ ያወጣ ግዙፍ ማንነት ይዞአል፡፡ ጭራሽ ወደፊት የኢንተርኔት አክሰስ በአለም ላይ ነጻ መተላለፉ ስለማይቀር፤ ፌስ ቡክ በግሎባል የምንጠቀምበት እና በየሜዳው፤ በየጫካው በየከተማው በቤት ውስጥም የሰው ልጅ ግንኙነት የደራ ይሆናል፡፡ በሀሳብ በፖለቲካ አመለካከት  የሚገናኙ የአለም ሰዎች በዚህ መልኩ አብሮነት ይፈጥራሉ፡፡ ግሎባል ማለት ይህ ካልሆነ ምን ይሆናል?


ጉዳያችንን የምንካፈልበት፤ ነውሮችም ይፋ የሚገለጥበት እና፤ አንዱ ህዝብ ለሌላው ህዝብ የሚታገልበት መሆኑ የማይቀር ሀቅ ነው፡፡ ባዩሽ ይህንን ዘመን ታያለች ወይ የሚለውን ስናይ ደግሞ፤ ምንአልባት ነው፡፡ አለም በአፋጣኝ በቴክኖሎጂ እያደገች በመሆኑ፤ እነዚህ ነገሮች አመትም ባልሞላ ግዜ ውስጥ ሊፈጸሙ ይችሉ ይሆናል፡፡ አለም ባላወቅነው እርምጃ ወደግሎባል እየገባች ነው፡፡ ስደቱ፤ ሀብት ማካበቱ ኢንተርናሽናል እየሆነ እያየነው ነው፡፡ የአለም ህዝብ ወይ ሀብት በማካበት አልያም በስደት እየተዛመደ መጥቶአል፡፡  


የኢትዮጲያ የፖለቲካ ንቃተ ህሊና እና አለም የደረሰችበትን  ሁኔታ ለማወቅ ባጣነው ግንዛቤ ግን ባህሪያችንን እየጎዳነው አይምሮአችንን ፈታኝ በሆነ ጠባብነት እየገደልነው እንገኛለን፡፡ በዚህም የተነሳ ሰው መነጋገር ሳይሆን መሰዳደብ መዘላለፍ ይዞአል፡፡ እንደእውነቱ የተቃዋሚውም ሆነ የገዢው ፓርቲ ደጋፊ የሚያደርጉትን የሚያወቁ አይመስልም፡፡ አልያም ጊዜያቸውን በቡዋልት እና በፌዝ በማሳለፍ የለመዱ ናቸው ብዬ አስባለሁ፡፡ አንድ ነገር ግን የምናቀውቀው፤ ይህ በከፍተኛ ጥላቻ የተደገፈው መዘላለፍ ግን ሞራል የለሽ ነገርም ሲተላለፍ የማህበራዊ ሚዲያውን አጠቃቀም ያላወቁ ሲበክሉት እያየን ነው፡፡  እኔም ዘግቼ የማላልፈው ጉዳይ ሆኖብኛል፡፡ እያንዳንዳችን ሕብረተሰባችንን መጠበቅ የግድ ተከፋይ ወይም ወገንተኛ መሆን የለብንም፡፡ ሰው ሰው ሆኖ ማለፍ አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ ሰው ጅራት የለውም፡፡ ሰው የማያደርገው ሌላ ተቀጥያ ነገር የተፈጠረው በተፈጥሮአዊ ይዘቱ ሳይሆን ባህሪው በፈጠረለት ብቻ ነው፡፡  


በእርግጥ ኢትዮጲያ ከባድ ፈተና ላይ እንደምትገኝ ተቃዋሚም ሆነ ገዢው ፓርቲ የሚክድ አይመስለኝም፡፡ እኛም እያየነው ነው፡፡ ሁሉም ፖለቲከኞቻችንን በዚህ ነገር ሀላፊነቱ ጠምዶአቸው ይገኛል፡፡ ምንአልባት ልባቸው ሀላፊነትን የፈራ እና የተጨናነቀ ሊሆን ይችላል፡፡ በማንኛውም ወቅቱ የትላቻው መናር ሰብሮ ሊወጣ የሚችለው ነገር ሊኖር ይችላል እና፡፡ እኛ ጥቂቶቻችንን ግን ሀላፊነት በጎደለው መልኩ፤ ለማንኛቸውም አጋዥነት የሚሆን ባህሪ መፍጠር አልቻልንም፡፡ የተቃዋሚ ደጋፊ ገዢ ፓርቲውን፤ የገዢው ፓርቲ ደጋፊ ተቃዋሚውን ስለሰደበለት አይደለም የምትረዱዋቸው፡፡ ይህ ሁኔታችሁ የሚያሳየው የእራስን ጋጥ ወጥነት ብቻ ነው፡፡ እነዚህ ሁሉም ግን ኢትዮጲያዊ ናቸው ብዬ አምናለሁ፡፡ ጣት ገማ ተብሎ ተቆርጦ አይጣልም የሚል አባባል አስታወስኩ፡፡ ታዲያ እነዶ/ር ብርሃኑም ሆነ እነ አቶ መለስ ዜናዊ፤ ተመቸንም አልተመቸንም የፖለቲካ አላማ ይዘው የተነሱ እንጂ ይህ በፌስ ቡክ እንደሚተላለፈው በሴት እራቁትነት፤ አልያም  ልቅነትን በሚያሳይ ምስል ላይ ሊቀመጡ የሚገባቸው አይደሉም፡፡  ይህ አንዳንዶች የምትልኩት ልቅነትን የሚያበረታታ እንጂ በምንም መልኩ የእነዚህን ኢትዮጲያውያን ወገኖቻችንን ባህሪ የሚያሳይ አይደለም፡፡ ጥቂት ሰዎች በድግግሞሽ ወጣቱን አቅጣጫ እንዲስት የሚያደርግ የቆሸሸ ምስል ማስቀመጥ እና በማህበራዊ ሚዲያ ማቅረብ ሁላችንም ልንቃወመው የሚገባ ሀቅ ነው፡፡  ይህ እርኩስ ባህሪ የሚያሳየው የእናንተን ጋጥ ወጥ ባህሪ እንጂ ተቃዋሚንም ገዢ ፓርቲውንም ባህሪ አያሳይም፡፡ ሁሉም ተሳሳቱም ጥሩ ሰሩም፤ ያንጸባረቁት በእኛ ውስጥ የሚጉላላውን የኖረውን ወደፊትም የሚኖረውን የፖለቲካ ፍላጎታቸውን ነው፡፡ እነዚህን ሰዎች ልቅነትን በያዘ ምስል ላይ እነሱን ለጥፎ ማቅረብ ግን መላው የኢትዮጲያን ህዝብ እንደመሳደብ እንደመኛቅ ይቆጠራል፡፡ ስለዚህ ይህንን የምታደርጉ ሰዎች፤ ከዘመናዊነትም ጋር፣ ከዜግነትም ጋር፣ ከፖለቲካም ጋር፣ ከማህበራዊ ሚዲያ ጋር ምንም ግንኙነት የለውም፡፡ ባለድረገጾች ሊያስተውሉ የሚገባቸው፤ ድረገጹን ለምን ብለው እንደከፈቱት ማሰብ መልካም ይሆናል፡፡  ስለዚህ ወደጤነኛ የሆነ የፖለቲካ ንግግር ቀርባቸሁ፤ በዳዴ የሚሄደውን የወያኔን ዲሞክራሲ ወይ ለማሳደግ መጣር፤ አልያም 60% እንኩዋን ዲሞክራሲ እንዲኖር መታገል ነው፡፡ ሀግ ባይ የለለበት አገር ወጣቱን አቅጣጫ የሚያሳየው ጠፍቶአል እና፡፡
ባዩሸ

Sonntag, 22. Februar 2015

ዘመነ ኢሕአዴግ „ አለም „ ተከፍታ ለኢትዮጲያውያን ተለቀቀችለት



ዘመነ  ኢሕአዴግ „ አለም „ ተከፍታ ለኢትዮጲያውያን  ተለቀቀችለት

አንድ ነገር አለ፤ ኢትዮጲያ በአለም ዙሪያ የምትታወቀው በኢኮኖሚዋ ደሃ ተብላ ነው፡፡ ብዙ ግዜ የሚነገረውም ከሕዝቡ ቁጥር ግማሽ ያህሉ ጭራሽም ጠግቦ የማያድር፤ እናት ለልጁዋ ይቅርብኝ ብላ ሳትበላ እንደምታደር ይነገራል፡፡ እንኩዋን በያይነቱ ልብስ ሊቀያይር ቀርቶ የእለት ጉርሱን ለመሙላት ደፋ ቀን የሚል ነው፡፤ ማንም እስካልተጎራ ድረስ በቤታችን ውስጥ ብዙ ጎዶሎ እንዳለ አንክደውም፡፡ እንዳውም በአንድ ቤተሰብ ውስጥ ብዙ ግዜ አንድ ወይም ሁለት ብቻ ሰራተኝ ነው ገቢ ያለው ፡፡ በቤተሰባቸው ውስጥ የሁሉም ሃለፊ ሆነው ጫና እንደሚበዛባቸው ነው፡፡ ሌላው ስራም የለውም የእሱን እጅ ብቻ ቁጭ ብሎ መጠበቅ ነው፡፡ ይህ ለእይታ ተጠጋግቶ መኖር ፍቅር ያስመስለዋል፡፡ አይደለም አንዱ የሌላው ጥገኛ ስለሆነ ነው፡፡ አንዱ ካለአንዱ መኖር ስለማይቸድል ነው፡፡ በፈረንጅ አገር ልጆች ወላጆቻቸውን አይጠይቁም ይባላል፡፡ እርግጥ ነው ብዙውን ግዜ ይህ ይታያል፡፡ ግና እውነቱን በቅርብ ሆኜ እንደተረዳሁት፤ ችግር ስለለለ አንዱ የአንዱ ጥገኛ ስላልሆነ ብቻ እንጂ የጥላቻ ባህል ኖርዋቸው አይደለም፡፡ የፈረንጅ ልጅ 18 አመት ሲሞላው ከቤተሰብ መገንጠል ያለ ነው፡፡ የእራሱን ህይወት መመስረት ያለ ነው፡፡ በእኛ አገር ግን ይህ እንዳይሆን ድህነቱ ጥገኛ አድርጎታል፡፡ ብዙ ሰው እንዳውም ለትዳር እንኩዋን ሳይታደል በእናት አባቱ ቤት ጎልማሳነቱን የሚያቃጥለው ብዙ ነው፡፡ከነበረበት ቤት እንዳይለቅ አልያም እንዳይወጣ፤ ጎጆ የመቀየስ ችሎታ የለውም፡፡ ገቢ ይላልእና፡፡  ስራ የለውም ወይ ቤት መስራት አልያም መከራየት አይችልም፡፡ እንግዲሕ የውጮቹ ብዙውን ግዜ ስለኢትዮጲያ ድህነት  ሲናገሩ፤ የጠላት ወሬ የሚሉ የአገራችን ሰዎች ሞልተዋል፡፡ አይደለም እውነቱ ግን ይህ ነው፡፡ ብዙ ሰው በባዶ ሆዱ ያድራል፡፡ የእግዚአብሄር ጥበብ ስላለበት፤ የቀን ኑሮውን እንዲሁ እየተጠጋጋ  መኖር ያለ ነበር፡፡ መቼም የጉድ ነው እንዴት እንደሚኖር፡፡ የውጮቹ ጻፉት እኛ ግን በየቀኑ እያየነው ነው፡፡ አዎ ጠግቦ የማያድር ደሃ ነው፡፡


ይህ ለብዙ ግዜ የቆዬ ቢሆንም፤ በሀብታም እና በድሃ መካከል ያለው ልዩነት እጅግም እንደዛሬው ጎልቶ የታዬ አልነበረም፡፡ ብዙ ማተሪያል ባልታየበት ወቅት ብል ይሻላል መሰል፡፡  በኢሕአዴግ ግዜ ብዬ ተቃዋሚውን የማስደሰት ንግግር እንዳይሆን፡፡ ያነዬ ፤ እከሌ ደሃ ነው እከሌ ሀብታም ነው የሚባል የተጋነነ ወሬ አልነበረም፡፡ ሙስናውም በገንዘብ የተወሰነ ሳይሆን ምንአልባት አንገትን በመድፋት እና ትህትናን በማሳየት ነበር ብዬ እገምታለሁ፡፡ ዛሬ ግን ይህ ድህነት እስከነአካቴው ጦም አዳሪእና በረንዳ የወደቀ አፈራ፡፡ ለምን ቢሉ አግበስባሹ በእጅጉ እያሻቀበ በመውጣቱ ነው፡፡ ሙስናው ደራ፡፡ „ ለብሳ የማታቀውን የሰው ጃኖ ለብሳ፤ ነይ ተመለሽ ቢሉዋት ወዴት ተመልሳ“  ሆነ ነገሩ፡፡ ያ አንዱ የአንዱ ጥገኛ ሆኖ ሲኖር የነበረውም ብልተጥ አመጣ፡፡ ለምን ብዬ ወንድሜን እህቴን ሌላውን በላለሁ ተባለ፡፡ ሰበካውም ይህ እንዲጠፋ እና እርስ በእርሱ የጎሪጥ እየተያዬ ዘመኑን እንዲያማርር መሰለ ነገሩ፡፡ ሰነፍ እና ጎበዝ በማለት ለዩት፡፡ ስራ ያልተሳካለት ሰነፍ ተብሎ ተፈረደበት፡፡ ስራ እንደምንም በተለያየው ሙስና ስራ የተወሸቀው ጎበዝ የተነቃቃ እየተባለ ይሞገስ ጀመር፡፡ ደሃ በሆነች አገር የስነልቦና ናዳ ሆነ ዳቦው፡፡

ከመሬቱም  መፈናቀል መጣ፡፡ በጠገኝነቱ መረዳዳቱ ቀርቶበት፤  አውራውም ልቀቅ ሆነ፡፡ መሬቱም ማምረቻ ሳይሆን ልማቱ በሚሊዬን እየሸጡ የእራስን ኬስ ማዳለብ ሆነ፡፡ አንዳንዱ መሬት አምስት ስድስት ግዜ በትርፋማ ገንዘብ መቸብቸብ ሆነ፡፡ መሬት የኢትዮጲያ አልማዝ፤ መሬት የኢትዮጲያ ቤንዚን ሆነ፡፡ እከሌ ከበረ ተባለ እንጂ የሀብት ቁጥጥር ኢህአዴግ አያውቃትም፡፡  ገንዘብ ገንዘብ ብቻ፡፡ ምን ገዶ፡፡ እምነትም ይህን የማይቃወመው በንዋይ ማደግ ትክክለኛ መሆኑን መሰበክ ያዘ፡፡ ገንዘብ ገንዘብ ንዋይ ንዋይ፡፡ ለኢትዮጲያዊ  በዘመነ  ኢሕአዴግ  አለም ተከፍታ ተለቀቀችለት ፡፡ ሁሉም በተከፈተው በር ገባ፡፡ አለማዊም ሆነ፡፡  ከተማ ወደላይ ማደግ ሲገባው፤ አዲስ አበባን እንደላስቲክ ለጠጡዋት፡፡  ቢሚሊዬን ያጠራቀሙ ዛሬ አዲስ አበባን ወደላይ እንገንባት ያን አፍርሱ ይህን አፍርሱ ሆነ፡፡ ከምንየው አዲስ አበባ በየሜዳው እንደልቡዋ ሄዳ፤ አዲስ አበባን ትልቁን ከተማ ሳይሆን ትልቁ መንደር ሆነች፡፡ ሁሉም  አዲስ አበባ በሆነበት ኢትዮጲያ፤ የቻለ ሙልጭ እያለ ገባባት፡፡ ፊንፊኔ ተጨናነቀች፡፡ የቻላ የሚያገኝባት የሚከብርባት ትንሽዋ ሳውዝ አፍሪካ ልትሆን፤ ወንበዴም የሚፈጠርባት ሆነች፡፡ እንአቶ መለስም ሙስና ዋጠን ማለት ያዙ፡፡ አፍ እንዲከፍት የሰለጠነው አውሬ ዋጠን ቢሉት ምንዋጋ ነበረው፡፡ የቁራ ጩሀት ሆነ፡፡

 ሲሮጡ የታጠቁት ሲሮጡ ይፈታል እንዲሉ፡፡ ብርን መከመር በኢትዮጲያችን ፤ ስንቱ ጦም ባደረባት  ተፈጠረ፤ ገደብ የለለው ልዩነት ተወለደ፡፡ እኔ ብቻ ልኑር፤ የእኔ ብቻ ዘመድ ዘር ይኑር መጣ፡፡ የገንዘብ ሰው ሲፈጠር የሚርበው እየበዛ እንደሚሄድ ጥርጥር የለውም፡፡ ዛሬ የኢትዮጲያ ሕዝብ ድህነት በእጅጉ አሻቅቦአል፡፡ ዛሬ የአማኝም ሀብታም ተፈጥሮአል፡፡ የሚያካብት፤ አንቱ የሚባሉ፡፡ ድሮ መስቀሉን ይዞ ግብረገብ ያስተምር ነበር ቄስ፡፡ አዎ ግብረ ገብ እና ስብእናን፡፡ ሙስሊሙም የሰው ሀቅ አይነካም ሲባል እኔ እንኩዋን ደርሸበታለሁ፡፡ ዛሬ ያ ሁሉ መከባበር አፈር ድሜ ገባ፡፡ አንዱ አንዱን እየሰደበ እየከሰሰ ኪሱን መሙላት ሆነ፡፡ እርግጥ ነው፡፡ የአንዱ ሀብታም መሆን የሌላው ድህነት ነው፡፡ ልብ ብሎ ላስተዋለው፡፡
ባዩሽ

Freitag, 20. Februar 2015

ትዝታ



ትዝታ

ያንን መገፋቱን ምንአልባት ብችለው
እስኪ መቀነቱን ስጡኝ ልታጠቀው
አገር አገር  አሉኝ፤ አገር እንደለለኝ
በኔ እየደነሱ ሁሉን ቀምተውኝ
ስጡኝ መቀነቱን ወገቤን ላጥብቀው
አልቻል ያለውን ብሶት እንድችለው
ዳዊቴን ሰቀልኩት አልደግምህም  ብዬ
እንዳያበላሸው ጠብ ሲል እንባዬ
 ጎበዝ አቀብለኝ ያን መቀነቴን
ጠበቅ ላድርገው ናፋቂው አንጀቴን
እንዴት ነሕ በሉልኝ ያንን ላሊበላ
ጌታ ከፈቀደ አይዋለሁ ሁዋላ
 ጊሸን ማሪያም ሂዱ እስኪ ንገሩዋት
ከርሜአለሁ እና ሄጄ ካየሁዋት
መቁዋሚያየን ስጡኝ ደግፍ ልበለው
የደሴን ሚካኤል በርቀት እንዳየው    
ያለፍኩትን ሁሉ አልፎአል እንዳልለው
እየተካ እምቢአለ ቀኑ መናጢ ነው

ባዩሽ

Sonntag, 15. Februar 2015

ሞራል ያልተጻፈውን ሕግ ስለመጠቀም




ለወጣቶች፤  
ሞራል ያልተጻፈውን ሕግ ስለመጠቀም

ባለ ድረገጾች ድረገጻችሁን ትንሽ ጎብኘት አድርጋችሁ ለኢትየጲያውያን ብሎም ጤነኛ የሆነው የአለም ክፍል ህዝብ ማየት የማይፈልገውን ሞራል የለሽ ፖስተሮችን አስወግዱ፡፡ ወዲያው ለማጥፋት ሞክሩ፤ ይህ አይደለም አለም የሚያስፈልጋት፡፡ ሞራል እና ስብእና ነው፡፡ ይህን የሚልኩ ሰዎች በጣም በከፍተኛ ደረጃ በፍራስትሬሽን የወደቁ በመሆናቸው ጤነኛ የሆነ ሰው ማየት አይፈልግም፡፡ ማንኛውም እምነት፤ ደግሞም ማንኛውም ሕብረተሰብ በዚህ በኩል አንድ አይነት ባህሪ አለው፡፡ ስድነትን አይፈልገውም፡፡

ባለድረገጾች ጤነኛ ያልሆኑ ነገሮችን ከድረገጻችሁ ውስጥ አውጡ፡፡ ይህ ፈረንጅም ሆነ ማንም ጤነኛው ህብረተሰብ አይፈልገውም፡፡ የብዙ ፍራስትሬሽን የሆኑ ሰዎች አዘቅጥ ውስጥ የገቡ ፖሰት ካርዶችን ወዲያው ለማጥፋት ሞክሩ፡፡ ካልሆነ ይህንን የማያደርጉ ከሆነ ጤነኛ የሆነው ኢትዮጲያዊ ወይም ኤርትራዊ ከድረገፁ ይለይ፡፡ ኢትዮጲያም ሆነ ኤርትራ ወይም የአለማችን ሕብረተሰብ በዚህ ችግር የለውም፡፡  የሴክሹዋል ችግር ያለበት ህብረተሰብ አይደላችሁም፡፡ እንደሚመስለኝ፡፡ በስመእግዚአብሄር የምጠይቃችሁ  እራሳችሁን ከዚህ መቅሰፍት ለዩ፡፡ ከዚህ አይምሮን እየሰረቀ ሰውን ወደእሳት የሚልክ የሰይጣን ባለአደራዎች እራቁ፡፡ ለተሻለ ነገር አይምሮአችሁን አይናችሁን አውሉት፡፡ ማንም ጤነኛ አይምሮ ይህንን ያውቃል፡፡ ተስፋ የቆረጠ ሰው ሊያደናግሩዋችሁ  ከሚራወጡ የሰይጣን ፈረሶች እራቁ፡፡ እነሱ ምንአልባት እንደተለከፉ ላይታወቃቸው ይችላል፡፡ ይህ በሁለት ሰዎች የሚፈጸም እንጂ ለሌላ የሚተላለፍ አይደለም፡፡

እናንተ ግን ጤነኛ ናችሁ፡፡ ግዜያችሁን ሊገልባችሁ ሰይጣን ይነሳል እና እወቁት፡፡ እሱንም ገስጹት፡፡ በፈረንጅ አገር እንዲሕ አይነት ነገር በሶሻል ሚዲያ አይለቀቅም፡፡ ለእንደዚህ አይነት ሰዎች ለእራሳቸው ተከልሎላቸው የተገሉሉ የተናቁ ሆነዋል፡፡ ፈርንጅ ይህንን ሲያይ የሚውል አይምሰለህ፡፡ የተሳሳተ ፕሮፖጋንዳ እየተከተላችሁ እነዚህ ሞራል የለላቸው ነገሮች ስልጣኔ አይምሰላችሁ፡፡ የለም ይህ የፈረንጅ ስልጣኔ አይደለም፡፡ ስልጣኔያቸው፤ ዳቦዋቸውን እኩል ማካፈል መስራት እና ዲሞክራሲያቸው ላይ ማተኮር ነው፡፡ ሰባኣዊነትን ነው ወጣቱ የሚያውቀው፡፡ ነውር ነገሮች የሚተላለፉት የእራሳቸው ሚዲያ አለ፡፡ እዛም ከ18 ዓመት እድሜ በታች ትውር አይልም፡፡ እዚህ የእናንተ ሶሻል ሚዲያ ግን እንደልቡ እያደረጋችሁት ነው፡፡ በልጅ እና በአዋቂ መካከል ያለውን እድሜ ክልል አክብሩ፡፡

ሰላሳ አምስት አመት ፈረንጅ አገር ስኖር፤ ስድ የለቀቀ ነገር በእኔ አካባቢ የለም፡፡ እነዚህ ጥቂት ስድ የሆኑ ሰዎች የሚኖሩት በተከለለላቸው አካባቢ ብቻ ነው፡፡ እሱም ቢሆን የፈለገ፤ ወደዛ መሄድ ይችላል እንጂ የማይፈልገውን መበከል አይፈቀድላቸውም፡፡ ለምሳሌ አንድ ነገር አለ በኢትዮጲያውያኖች አካባቢ የሚነገር፤ ፈረንጅ በየሜዳው ፈሱን ይፈሳል የሚባል፤ ስህተት ነው፤ እኔ ይህንን በጀርመን አይቼ አላውቅም፡፡ የማንንም ፈስ ተጋሪ ሆኖ የሚያሸትም ህብረተሰብ የለም፡፡ አምልጦት እንኩዋን አንዱ ቢለቀው፤ የእሱ ባለማስመሰል ይሆናል እንጂ፤ ጣት እስከምንቀስር ድረስ አያደርገውም፡፡ እንኩዋን እግሩን አንስቶ ሊፈሳ ይቅር እና፡፡ ነውር የሆኑ ባህሎች የሚታወቅበት አገር ነው፡፡ ማግሳትም ትልቅ ነውር ነው፡፡ አፍንጫን ሳያፍኑ ማንጠስ እንኩዋን ብዙ ትችት እና ትዝብት ይሆናል፡፡

ሰሞኑን በሚዲያ የሰማሁት ምክር አለ፡፡ እሱም ሚኒስከርት ለብሳችሁ በአውቶብሱ ወይም በባቡር ውስጥ መቀመጥ እንዴት አስቀያሚ እንሰደሆነ እና ሰዎች ይህንን በመዘንጋት ስለሚያደርጉት እንዲጠነቀቁ ይናገር ነበር፡፡ ሴት ብቻ አይደለም ወንዶችም ቢሆን ተንፈራጦመቀመትን የማይበረታታ ይሉታል፡፡ በአጠቃላይ በህዝብ ትራንስፖርት አቀማመጥን እንኩዋን በተመለከተ ሲያስታውሱ እና ቲፕ ሲሰጡ ነበር፡፡ የተበላሸ ኖሮ ብቼ ሳይሆን፤ እንዳይበላሽ፤ ከጊዜ ብዛት ነውር የሆነውን እንዳይረሳ፤ ሪፖርተሮች ያሳስቡ ነበር፡፡ ልብ ብለንም ስናይ ይህንን የሚያደርግ እጅግም ብዙ የለም፡፡ ሁሉም በፖርሳው የነውርን አካባቢዎች ሸፈን በማድረግ ይቀመጣሉ፡፡ ፊት ለፊታቸው ሌላ ሰው ስለሚቀመጥ መረበሽ እና አቅጣጫን ማሳት ነው ይላሉ፡፡ ለሁሉም ነገር የሞራል ገደብ ባልተጻፈ ህግ የተደነገገ መሆኑን ሁላችንም እናውቀዋለን፡፡ ይህንንም ሰው ይጠቀምበታል፡፡ ያውቃል፡፡ ካልሆነም በተመልካች አካባቢ ግልምጫ እና መሳቂያ ወዲያው በማድረግ፤ ሰው እርስ በእርሱ በመተያየት የማይዋጥ ነገር እንዳደረገ ያሳዩታል፡፡ ስለዚህ ወጣቶች ፤ያልተጻፈ ሕግ እንዲሁ በተፈጥሮ ውስጣችንን ያነቃቃን የእግዚአብሄር ነገር አለ እና ይህንን እንፈጽመው፡፡ እንዳው ፌስ ቡክ ስሜን መልኬን ስለቀየርኩ ማንም አያውቀኝም በማለት እንዳገኛችሁ አትሁኑ፡፡ እውነቱ አንድ ነገር ነው፤ እሱም እግዚአብሄር በስምህ ሳይሆን በማንነትህ የሚሰራ አምላክ ነውእና አሳችነትህ ለእሱ ድብቅ አይደለም፡፡ በአለም ላይ ያለው ያልተጻፈ ሕግ፤ ሁላችንንም በአንድ የባህሪ ባህል ያገኛኘናል፡፡ እሱም ሰው የተባለ ፍጡር ክፉና ደጉን ያውቀዋል፤ ተደብቆም የሚያደርገው ለዚህ ነው፡፡ ሰላም ይብዛላችሁ ባዩሽ ነኝ፡፡