Samstag, 10. Mai 2014

በለስ የቀናው ፓርቲ?



በለስ የቀናው ፓርቲ?

ሁላችንም ለመልካም አስተዳደር መታገል እንችላለን፡፡ ግን ፖለቲከኞቻችን የሚሆኑት በጣት የሚቆጠሩ ጥቂቶች ናቸው፡፡ እነሱም የፖለቲካ ጥበብ የተሰጣቸው የተካኑ የተማሩ መሆን አለባቸው፡፡ ከእንግዲህ በሁዋለ ሁሉንም ማግበስበስ የለብንም፡፡ ባለሙያ ፖለቲከኛ በአገራችን አያስፈልጋትም ያለው ማንነው? የሚጠቅመንንም ፓርቲ አስቦእና አስተውሎ መደገፍ እና ለዛ ፓርቲም መቆም ጠቃሚ ዋንኛ መንገድ ነው፡፡ ካልሆነ በበረት ውስጥ እያለች የፈረጠጠች ጥጃ ወይም የማይጨበጥ ህልም አላሚ ቅዠታም እንሆናለን፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ፣ አንድነት፣ ግንቦት 7 እና እራሱ ወያኔ ኢሕአዴግም በተደጋጋሚ ሲጠሩ  እሰማለሁ፤ እነዚህ ፓርቲዎች እንግዲህ በጭራሽ በአንድ ላይ ሆነው የተቀራረበ ስራ ሊሰሩ አልቻሉም፡፡ ግን እንደማየው ሁሉም እንደየመጠናቸው የሚፈልጋቸው ሕዝብ ያላቸው ፓርቲዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ አሁን ያዋጣል ብዬ የማስበው ነገር አለ፡፡ እሱም እነዚህን ፓርቲዎችን እንደምንም  ማወዳደር ነው፡፡ ለመወዳደር ግን የሚመቸው የህዝብ ለውጥ መፈለግ ብቻ ሳይሆን መደራጀትም ነው፡፡ በእርግጥ ወያኔ ኢሕአዴግ የሚመርጠውን ለማደራጀት ወይም ለመስበክ በለስ የቀናው ድርጅት ነው፡፡ ሚዲያውም አገሩም በእጁ ሆኖአል፡፡ ህዝብን በእጁ ማድረግ ደግሞ ካቃተው ችግሩ የእሱ ነው እንጂ የተቃዋሚ ሊሆን አይችልም፡፡ ተቃዋሚ ህዝብን ለማደራጀት የሚከብደው ነው፡፡ ግን ደግሞ የማይቀናው ነው ለማለት የሚዳግት ሁኔታ ላይ ገብተናል፡፡ ይህም በምኑም በምኑም ሕዝብ እየተሰላቸ እና ያለውን አስተዳደር እየኮነነ እየሄደ ነው፡፡

 በአገር ውስጥ ያሉ ፓርቲዎች በይፋ እየኖሩ ይገኛሉ፡፡ ግን ደግሞ አባሎቻችን እየታሰሩብን ነው ይላሉ፡፡ ሁለቱም የሚጋጭ ነገር ነው፡፡ ለምሳሌ በይፋ ከተንቀሳቀሱ እና አባል ከታሰረባቸው፤ የተሰጣቸው ሊሚት አለእና ያንንም እንዳታልፉ የተባሉ ይመስለኛል፡፡ ስለዚህ ከዚህ መታዘዝ ወጥተዋል ማለት ነው፡፡  ያንን ቃል የተሰጣቸውን ነገር ማፍረስ የለባቸውም፡፡ ካፈረሱ ችግራቸው የራሳቸው ነው፡፡ ልብ በሉ ገደብ ካለህ ወይ ትቀበላለህ ወይም አትቀበልም እንጂ ዘወትር አባሎቻቸው እየታሰሩ ዲሞክራሲ የለም እያሉ መጮሑ አባል እያደር ያሳጣቸዋል፡፡ ምክናያቱም ሰው ሲታሰር ሲደበደብ እያየ የሚገባ ኢትዮጲያዊ ስንቱ ነው ብሎ ማሰብም ተገቢ ነው፡፡ እንኩዋን ሲደበደብ አይቶ ተቃዋሚን ማነጋገር የሚፈራ እኮ ብዙ ነው፡፡ ለምሳሌ ባለፈው የተደረገው የአንድነት ሰላማዊ ሰልፍ ሀይለኛ ብዙ ሰው ያካተተ ነበር፡፡ የበቀደሙ ግን ከዛኛው በእጅጉ አንሶአል፡፡ ስለዚህ ሰው ተስፋ ቆርጦአል ወይም በፓርቲው እምነት አጥቶአል አልያም ፈርቶአል ማለት ነው፡፡

እንግዲህ ይህን እንዳለ ልተወው እና ግንቦት 7 የሚባለውስ፡፡ እሱ ደግሞ በአገር ውስጠ ገብቶ ሊወዳደር የማይችል ፓርቲ ነው፡፡ እሱም ከመጀመሪያውም እንደምሰማው ዲሞክራሲ የለም እና ለምርጫውም ግባም ቢባል እንደማይገባ አይነት ነገር ነው፡፡ ኢህአዴግን በጭራሽ አያምነውም፡፡ ኢህአዴግም ግንቦት 7ን አያምነውም፡፡ ሁለቱ ቀንደኛ ተጻራሪዎች ሆነዋል፡፡ አሁን አሁን ደግሞ ፤በአገር ውስጥ ሌላውስ ተነቀሳቅሶ ያመጣው ምንድን ነው ብለውም የሚጠይቁ ብዙዎች ሆነዋል፡፡ ሕዝብስ ይደግፈው ይሆን የሚለውን ደግሞ ስዳስሰው፤ 70% ቱ ህዝብ  ግንቦት 7 የሚባለው ድምጽን ይወስዳል ብዬ እገምታለሁ፡፡  ዲሞክራሲ  የለም፣ ህዝቡም የመናገር መብት የለውም፡፡ ስለዚህ የሚናገርለትን የጠላቴ ጠላት ወዳጀ ነው ማለቱ አይቀርም፡፡ ማን ይጠላልእና ጠበቃ፡፡ በኢህአዴግ ችላባይነት የተሰላቸው ሰው፤ አማራ፣ ትግሬ ኦሮሞ…. ከሚለው አልፎ በዛው ውስጥ በጎጥ ተከፋፍሎ ቅጥ አምላኩ ጠፍቶት ሲያዩ ተስፋ ይቆርጣሉ፡፡ ግንቦት 7 ማደራጀትም የሚያስፈልገው ድርጅት አይደለም፡፡ ሰማያዊ ፓርቲም ሆነ አንድነት ፓርቲ የመሳሰሉት በሚደርስባቸው መንገላታት ግንቦት 7 የሚናገረውን የኢህአዴግን ኢታማኒነት እውነት አድርጎለታል፡፡ እሱም „ ዲሞክራሲ የለም ነው“ ፡፡ እና ህዝብ ምን ጥፋት አለው? በጆሮው የሚሰማው በአይኑ እያየው ነው፡፡   አንድነት ፓርቲእና ሰማያዊ ፓርቲ ሁልግዜ ከማሳሰር ውጪ አመርቂ ነገር ሊያስገኙ አልቻሉም፡፡ ሰላማዊ ትግላቸውንም ኢሕአዴግ በመልስ እንኩዋን  አውንታዊ መልስ አልሰጣቸውም፡፡ እሰየው እስኪ ዛሪ ይህን ላድርግልህ አላላቸውም፡፡ ጭራሽ ዳርዳሩን እንዲሄዱ እያደረጋቸው ነው፡፡ በዚህም የተነሳ ህዝብ ቀስ እያለ አይኑን ሊያነሳ ይችላል ብዬ እገምታለሁ፡፡ ሌላው በዘር የተደራጀው ሁኔታም አመርቂ ነገር ሳይሆን የሚያስጠላ መሆኑ ከቀን ወደቀን የተማረው ክፍል፣ዘመናዊው አስተሳሰብ ያለው ወጣቱ፣ ግሎባል ማይንድ የያዘው ሰው  እና በእምነት የሚጉዋዘው ክፍል እንዳለ እየጠላው ሄዶአል፡፡ ይህንንም ነገር ኢሕአዴግ ሊያገናዝበው እና እርመት አድርጎ ሊያስተካክለው አልቻለም፡፡ በዚህ የተነሳ ግንቦት 7 በለስ የሚቀናው ድርጅት እየሆነ መጥቶአል፡፡ የታዘብኩትን ጻፍኩ እንጂ እኔ እንደሁ ማንንም አላውቅም፡፡ ምክናያቱም ቤቴንም አንኩዋኩቶ ደግፊኝ ብሎ የመጣብኝ የለም፡፡ ስብሰባም ሲጠራ በአካባቢዬ አይቼ አላውቅም፡፡ ወይ ስብሰባ አለ መባሉን እኑካውን ብንሰማ አድራሻው አይታወቅም፡፡ ያው የተለመደ ባህል አለ አይደል ያልተለወጠ፤ ሁሉም የሚያምነውን እንደኢሕአዴግ መጥራት፡፡ እኔ ግን እንደፈለጋቸሁ ተቹኝ እንጂ፤ ማንም ቢጠራኝ እሄድ ነበር፡፡ እረ ያሉበትንም ባውቅ፡፡ ግንዛቤ የሚመጣው እኮ በዚህ ነው፡፡ አይዞአችሁ፤ እኔ እንኩዋን ለመንግስትነት ለቀበሌም የሚሆን እውቀት የለኝም፡፡ ግን የሚገርማቸሁ እና የማትንቁት፤ ከተሹዋሚው ይልቅ የመራጭ ድምጽ ወርቅ ናት፡፡
በቸር የምትላችሁ፤ እራሱዋን ነጻ ያወጣችው  ባዩሽ ነኝ፡፡ አዎ ነጻነትን መጠበቁ ሰልችቶች እራሴን ነጻ አወጣሁት፡፡ ይህም መብት ነው፡፡ መቼም እስከቀኑ፡፡

Samstag, 3. Mai 2014

በዘር የተደራጀው እና ያልተደራጀው



በዘር የተደራጀው እና ያልተደራጀው

ሁሉም ሆድ ብሶታል፡፡ በዚህም መካካል ነጻ ሆኖ መናገር እየከበደ መጥቶአል፡፡ አቅጣጫውም እንዴት እንደሚሆን እንጃ፡፡ ገዢው ፓርቲም ቢሆን በሰው ላይ ተቆጣጣሪ ከመሾም በስተቀር አመት ሙሉ ምንም አይነት የፖለቲካ ግንዛቤ ለማስጨበጥ ያደረገው ነገር አልነበረም፡፡ ሁሉንም በትዝብት አልፌዋለሁ፡፡ ይህ ሁሉ ተቃዋሚ ምን ያመታሉ የሚለው ንቀት ነበር፡፡ ግን በየትም አለም ተቃዋሚዎች የሚያመጡት ነገር እንዳለ ለሁሉም አለም በገሃድ ይታወቃል፡፡ ይህ ባይሆን የምእራቡም ሆነ የምስራቁ አለም ተቃዋሚ የተባለውን ሁሉ ጥግ ባልሰጠው ነበር፡፡ አዎ ትክክል ነው፤ ቤተመንግስቱንም ቢከለከሉም ተቃዋሚ የለለበት እና ነጻ የማይንቀሳቀስበት አገር የሚኖር ገዢ ፓርቲ አዳጋች አቀበት ላይ ቆሞ ወደፊትም ወደታችም ለመሄድ ይቸገራል፡፡ ድህነት ባለበት አገር እና የሰው መበላለጥ በሚታይበት ኢትዮጴያ ተቃዋሚ ፈላጊ የለውም ማለት እንቅልፍ የለለው መተኛት ይሆናል፡፡ በዛም ላይ ደግሞ ኢሕአዴግን የወረረው የራሱ ፓርቲ አባል ለእራሱ ለኪሱ ሲል እንጂ ምንም አይነት የፖለቲካ ንቃተ ሕሊና እንደለላቸው ያየነው ነው፡፡ እነሱ የሚያደርጉት በቀላሉ ለኢሕአዴግ ተቃዋሚ እያበዙ ወደ ተቃዋሚ ፓርቲዎች መላክ ነው፡፡ በዚህ ተቃዋሚ ፓርቲ ሊድሰት ይገባዋል፡፡ እነዚህ የኢሕአዲግ አባሎች ግን የሚያደርጉት ድርጊት ከእራስ ፍላጎት የመነጨ እንጂ ለተቃዋሚ መደገፍ እንዳልሆነ ልብ ማለት ይገባናል፡፡ ስንናገር ተቃዋሚ ስንጮሕ ቀውስ እየተባልን ኢሕአዴግ ዘወር ብሎ ያላየው እጅግ ብዙ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ሊረዳው ያለ ብዙ ነበር፡፡ ግን ተቃዋሚ ምን ያመጣል የሚለው ደካማ እይታው ያልመለሰው ጥያቄ እንዳለ እና እጅግ እየተንገላታ እየተገለለ ያለ ዜጋ እንዳለ ማስተዋል አልቻለም፡፡ እኔ ስለደላኝ አንተ አፍህን ዝጋ ማለት የምንችልበት አለም ላይ አንኖርም እና፡፡

ጥያቄው ለእኔ ልማት የሚለው ነገር አይደለም፡፡ ልማት እጅግ በጣም አስፈላጊ እና አንገብጋቢ መሆኑን እኔ በበኩሌ አውቃለሁ፡፡ ደጋግሜ እንደምናገረው፤ መሬትን የምታፈራውን እንጂ የምንበላው መሬቱን አይደለም፡፡ ግን ኢህአዴግ ለዚህ ጉዳይ ወይ አንድ ናችሁ ብሎ በአንድነት ህዝብን እንደማደራጀት በየጎሳ ክልል ከልሎ ከልሎ የሰው ስነልቦና በሙሉ ኢሕአዴግን እንደዘረኛ እንዲታይ ያደረገው የዚሕ የጀመረው ሲስተም ነው፡፡ ችግሩ መሬት አይደለም፡፡ የሰው አይምሮው ግን ኢሕአዴግን ዘረኛ ብሎ ገንብቶ እንደሚገኝ ይህን በትክክል ለሁላችንም ግልጽ ነው፡፡ ለምሳሌ አማራው ክልል ላይ አዎ አማራዎች እንዲስተዳድሩ አልያም እንዲጠብቁ የተሰጣቸውን ስልጣን እያየነው ነው፡፡ ይህም ህዝቡን እንደልባቸው ከማንገላታት ውጪ አንድም ቀን ሰብስበው የኢሕአዴግን አላማውንም ሆነ ምኑንም አስታውቀውን አያውቁም፡፡ ሰውም ሲበደል ትክክለኛ ዳኝነት አያገኝም፡፡ ጭራሽ እራሱ በኢሕአዴግ ሲስተም የተቁዋቁዋመውን መዋቀር እራሳቸው ሲንቁት ነው የምናየው፡፡ ለመሆኑ ኢሕአዴግ ለዚህ ለፖለቲካ ስራው ብቃት ያለው ሰው አሰማርቶአል ወይ ብየ ስጠይቅ አላሰማራም አልያም ደግሞ ክልሉን እንዳለ ትቶታል፡፡ ማእከል የለለው አገዛዛ፤ ህብረተሰቡ ከፍርድ ቤት ፍርድ ቤት በመንከራተት ደግሞም ሕጉን ሳይሆን የምንፈራው አስከባሪውን መሆኑ ይህ ሁሉ ኢሕአዴግን እንዲናቅ አድርጎታል፡፡ ተከብሮ መኖር እና ተፈርቶ መኖር መቼም ልዩነቱን ማንም ያውቀዋል፡፡ ስለዚህ ኢሕአዴግ ፈተና ላይ የወደቀው በእራሱ አባል መሆኑን እያየነው ነው፡፡ አገሪቱን እውነት ኢሕአዴግ ማስተዳደር ከፈለገ የዘር ፖለቲካን አንድ ግዜ ደግሞ ማሰብ ግድ ይለዋል፡፡ ሊከፋፍለው አስቦ ከሆነ እንዳለ መተው ጥሩ ነው፡ ግን ኢትዮጲያን በአንድነት አስተዳድራለሁ ካለ ደግሞ ይህ አማራ ትግሬ የሚለውን ስም በጭራሽ ማጥፋት እና፤ በክፍለሀገር ወይም በክልል ማድረግ ትንሽም ቢሆን በሕብረተሰቡ መካካል አመኔታ ለመገንባት ጅማሮ ሊሆነው ይችላል፡፡ ካልሆነ ግን የዘር ክፍፍሉን ተቃዋሚ ነው ያመጣው የሚለውን ማንም ሰው ሊቀበለው የማይችልበት ምክናያት ለማየት ኢሕአዴግ አንድ እርምጃ ወደሁዋላ ብሎ አነሳሱን መሰለል አለበት፡፡ሁኔታውን ግን ተቃዋሚ ተጠቅሞበታል አዎ ስራ ነው፡፡ እንግዲህ ችግሩ እዚህ ላይ ነው የመጣው፡፡ በዘር የከፋፈለውን ክልል የአማራውን መሬት ወደ ሌላው የኦሮሞውን መሬት ወደሌላው ደግሞም የትግሬውን ወደሌላው ……..እያለ የሚያደርገው የልማት ህልም ካለደም እውን ላያደርገው ይችላል ብዬ ፍርሀት አለኝ፡፡ ምክናያቱም በዘር የከለልከውን ሰው መሬቱንም አሳልፎ ለመስጠት ይቸገራል እና ነው፡፡

በሌላ መልኩ በተደጋጋሚ የምሰማው ትችት፤ ተቃዋሚ በጎን ነገር እያጣመመ ህዝቡን ወደተቃውሞ እያመጣው ነው የሚለው አነጋገር የሞኝነት ነው፡፡ በየትኛውም አለም ተቃዋሚ ስራው የህዝቡን የልብ ትርታ አዳምጦ በዛ መሄድ ነው፡፡ ኢሕአዴግ ግን የህዝቡን የልብ ትርታ የሚየያቀርብለት የታመነ ሰራተኛ እንዳለው በጭራሽ አያውቅም፡፡ ይህም ምክናያቱም ከእያንዳንዱ ኢኮኖሚ ችግር የተነሳ ፖለቲካቸውን የተጠቀሙበት እራስን ለማውጣት ስለሆነ ነው፡፡ ይህን ኢሕአዴግ ቀድሞ ማወቅ ነበረበት፡፡ ድህነት ባለበት ወይም ሰው ጠግቦ በማያድርበት አገር ትክክለኛ የሚሸጥ ኢንፎርሜሽን ማግኘት እንዳማይቻል መረዳት ነበረበት፡፡ ለምሳሌ በጫካ ሆነው ከታገሉት ይልቅ ዛሬ ኢሕአዴግን የወረረው እውስጥ ቁጭ ብለው ሲጠብቁዋቸው የነበሩት እንግዳ ተቀባዮቻቸው ናቸው፡፡ የትግል ዋጋን የሚያቀው የከፈለው መሆኑ ሲታወቅ፤ ቀጥታ ከታገሉት ሰዎች አላማቸው ምን እንደሆነ በውል አላወቅነውም፤ ብዙዎቹ የሉም እና፡፡ ግን ጥቂቶቹን እንሰራላችሁዋለን ብለው እንደአጋዥ የከበቡዋቸው ከከተማ ወጥተው የማያውቁ ናቸው፡፡ ስራ ፈላጊም ደግሞም ፖለቲካ አዋቂም አብሮ ተሰልፎ የመጣውን ቀውስ እያየነው ነው፡፡ ተቃዋሚ ነው ብሎ ሰውን እንድይሆን ማድረግ እና ማሳደድ፤ ትክክለኛ ግብር ከፋይን ትቶ የሚያጭበረብረውን መደገፍ፤ ይህ ውነት ኢትዮጲዊነት አላማ ሳይሆን የኪስ ጉዳይ ነው፡፡ እንደእውነቱ በጌታዬ በእየሱስ ክርስቶስ ስም የምናገርው፤ ያየሁትን እና የተለማማድኩትን በመታዘብ ነው፡፡ ሁሉም ኢሕአዴግን የከበበው የፖለቲካ ንቃተ ህሊና የለለው ግን ከአገሪቱ ሁኔታ ወይም ድህነት የተነሳ ስራውን ላለመልቀቅ የሚታገል ነው ያለው፡፡ በዚህ የተነሳ ኢሕአዴግ ልማት ላይ አተኮርኩ ይበል እንጂ፤ የሚንድለት ያለው በእራሱ እጅ ያለው ነው፡፡ እንዳውም እንደምንም ብሎ ተቃዋሚ ጋር አብሮ ለመስራት ጥረት ቢያደርግ ከነገ እፍረት ይድናል ብዬ እገምታለሁ፡፡ እኔ ለእራሴ ቀውስም በሉኝ ጤነኛ በሕይወቴ ላይ የሚጫወተው ምንም አይነት ሚና የለም፡፡ ተቃዋሚም ደጋፊም አይደለሁም፤ በፖለቲካው አለም፤ ግን ንቃተ ህሊናው አለኝ ፡፡ ሁሉም ፖለቲካ እጅግ በጣም ያሳቀኝ በጣም በሳል ሌቦችን አጋዥ የሆነ ነው፡፡ ስለዚህ ለኢህአዴግ ግልጥ የማደርግለት ጉዳይ ቢኖር አባል ከሚያበዛ እና በመከላከል ብቻ እረጅም ግዜ ከሚኖር፤ አጥርቶ የፖለቲካ ስራ ቢሰራ መልካም ስም ባተረፈ ነበር፡፡ እኔ እንደማየው ኢሕአዴግ ሲገባ ከነበረው የዘር ፖለቲካ ለመውጣት እየታገለ ያለ ድርጅት ነው፡፡ ግን አሁን ትልቁ ችግር በዘር ያደራጁዋቸውን እና ቀድመው ያልተቀበሉዋቸውን አንድ ማድረግ ግን ፈተና ፈታኝ ሆኖአል፡፡ ሌላው የሚከፈለው ፖለቲከኛ አታካችእና አሳሳች ሲሆን ግን ፖለቲካን በሆቢ የሚሰራት አንድ ቀን ይወርሳታል እና፡፡ ለማንኛውም ለውጥን የምመኝ ሴት ስለሆንኩ የምታገለው እኔ ሰብአዊነት እና አጭበርባሪ ሰው እንዲታይ እንጂ ከፖለቲካ ጋር ምንም አይነት ግንኙነትም ፍላጎትም የለኝም፡፡ ግንስ መብትን ተገፎ ስላየሁት ለመብት የምትታገሉትን መልካም ሰዎች በሙሉ መንገዱን እግዚአብሄር ይከፍትላችሁ ዘንድ እመኛለሁ፡፡በቸር
ባዩሽ