Mittwoch, 10. Juni 2015

የሕይወት ውጣ ውረድ፤ ትግሬዋ ጉዋደኛዬ




           ስደት ይህችን አለም አሳይቶኛል፡፡ እኔም አይምሮዬ ግሎባል ሆኖአል፡፡ ግን አንድ በፈረንጆች ላይ ያየሁት ኩዋሊቲ ድንቅ የሚለው፤ ሰው ሲወድቅ የማይሸሹ፤ ሲያጣ የማይጥሉ፤ በህመሙ የሚገኙ እንባ የሚጠርጉ ናቸው፡፡ ይህም ለምድራቸው እንደበረከት ሆኖላቸዋል፡፡ የፈለገ ቢሆን ለደስታህ ላይገኙ ይችላሉ፤ ጋባዡም ቢቀር አይቀየምም፡፡ ግዜ ከለለው ግዜ የለውም ይላሉ፡፡ ግን በተከፋ፣ በአዘነ፣ በተሰቃየ እና ባጣበት ግዜ፤ ማንም ግዜውን መሰዋእት መውሰድ እንደግዴታ ነው፡፡ አስገዳጁ ግን ሕሊና ነው፡፡ እኔ ብዙ ያዘንኩበት ነገር ነበር፡፡ ስቃይም ነበረኝ፡፡ በዛን ሰአት ግን የተገኙልኝ ፍጹም የማላውቃቸው ያልተዋለድኩዋቸው ፈረንጆች ነበሩ፡፡ መጽናናትን አግኛቻለሁ ፍቅራቸውንም አይቻለሁ፡፡ ይሁን እና ግን እኔ ከወደድኩዋቸው፤ ካመንኩዋቸው እና ከጠበኩዋቸው የአገሬ ሰዎች፤ ከተወለዱኝም በወደኩበት ሰአት የቀረበኝ የለም፡፡ በታመምኩበት ሰአት የጠየቀኝ የለም፡፡ ይህን ስል ግን ስለ የኢትዮጲያን ዘጠና ሚሊዮን ህዝብ አይደለም የምናገረው፤ እኔ የምናገረው እራሴ ከጠበኩዋቸው ሰዎች ነው፡፡ እነዚህም ኢትዮጲያን ይወክሉ አይወክሉ አላውቅም፡፡ በባህሪ ደረጃ ነው የምለው፡፡ ብዙ ግዜ የወደቀን ግንድ ምሳር ይበዛበታል እስከምሳሌው ይባላል፡፡ እንዳውም በሕመሙም እና በድካሜ ወቅት ይስቁብኝ ነበር፡፡ ብቻየንም በመጣሌ ይዝናኑበት ነበር፡፡ እግዚአብሄርንም ለምን እያልኩ እጠይቀው ነበር፡፡ እሱም ብቻሽን ተውኩሽእን ያለኝ እስኪመስለኝ ፍቅሩን እሰማው ነበር፡፡ ለካስ እግዚአብሄር እነዛ የደረሱልኝን ፈረንጆች እያስነሳ ወደእኔ የሚልካቸው እሱ ነው ብዬ አመንኩ፡፡ ለካስ የእግዚአብሄር እጅ የሚታየው በረከት እንዲቀበሉ በፈቀደላቸው ሰዎች በኩል ነው፡፡ ሁሉ ለበረከት የታደለ አይደለም እና፡፡ እዚህ ሲስተሙም ሰውም የፖለቲካውም ስርአት በመከራህ ግዜ ብቻህን አይተውህም፡፡ እኔም እግዚአብሄርን አየሁት፡፡ በውነት አየሁት፡፡ ወገን ማለት በወደክ ግዜ ሊያነሳህ የሚታገል ነው፡፡ ወገን ማለት በታመምክ ግዜ አይዞህ አላበቃም ትድናለህ የሚልህ ነው፡፡ ወገን ማለት ስታለቅስ እቅፍ አድርጎ እያጽናናህ እንባህን የሚያብስልህ ነው፡፡ ባዘንክ ግዜ ብሶትህን የሚያዳምጥህ ነው፡፡ አዎ አይቸዋለሁ፡፡ በራፋቸው ሲዘጋ አይቻለሁ፡፡ አዎ ፊታቸው ሲጠቁሩብኝ አይቻለሁ፤ አዎ አብቃልሽ ከእንግዲህ ሰው አትሆኚም የሚለኝ አይቻለሁ፡፡ አዎ ብዙ አይቻለሁ፡፡ እኔ እንደከፉብኝ ሰዎች እንዳልሆን አምላኬ ትልቅ ትምህርት ሰቶኛል እና እኔ እንደእዛስ አልሆንም፡፡ ብችል አጽናናሃለሁ፡፡ ባልችል ግን በመከራህ ሰአት ፊትህን እያየሁ አልስቅብህም አልንቅህም፡፡ ቀን ተገላባጭ ነውእና፡፡ ሙስሊም የሆኑ ደጎችም አይቻለሁ፡፡ ይሁን እና ግን እኔ ክርስቲያን ነኝ፡፡ ደስታን አይደለም፤ መከራን፣ መጣልን እና መገለልን ያሳየኝን ክርስቶስ ግን አይቸዋለሁ፡፡ ስራው እረቂቅ ነው፡፡ አምላክ በጤነኞች ቤት፣ አምላክ በሀብታሞች ቤት፣ አምላክ ክርስቲያን ነን በሚሉ ቤት፣ አምላክ በደላቸው ቤት ብቻ ዘግቶ የሚቀመጥ አይደለም፡፡
              አንድ ግዜ የገጠመኝ አስመራሪ ነገር ነበር፡፡ ብቻዬን ነበርኩ፡፡ ቤቴ በዲንጋ ይደበደብ ነበር፡፡ ብዙ መገለል ደረሰብኝ፡፡ እኔ ያጠፋሁትን አላውቅም፤ ባውቀው በደለኞችን ለመቻል  መጽናኛ በሆነኝ፡፡ ተወልጄ ባደኩበት ኢትዮጲያ ደሴ መራራ ነገር እየኖርኩ እንዳለ ብዙው ህዝብ የሚያውቅ አልመሰለኝም፡፡ አልኮሆል አልጠጣም፤ የሰከርኩም አይደለሁም፡፡ ከህብረተሰቡ ባህልም የወጣ ልብስም አለበስኩም፤ ያደረኩትም ወንጀል አልነበረኝም፡፡ የሰውን ክፋት ያቺን ያየሁባት ወቅት ትገርመኛላች፡፡ አይኔ ሰው  ይፈልግ ነበር፡፡ አፍንጫየም ሰው በማሽተት ተርቦ  ነበር፡፡ ግን ሰው ጠፋ ሰው አልተገኘም፡፡ ጭራሽ የዲንጋው ውርወራ እና፤ ነይ በላይታችን ላይ ንጅብን እያሉ በጫት የደነዙ ወጣቶችም በመንገድ አላስኬደኝ አሉ፡፡ ስቃዬን ግን ስንቱ ያቀው ነበር፡፡ ለመሆኑ ያንን ለማየት እግዚአብሄር ካላሳዬ ማን ያየዋል፡፡
        አንድ ቀን  ታዲያ ወደመድሃኒአለም ቤተክርስቲያን ድንገት ሳላስበው አመራሁ፡፡ ቀኑ ሁሉ ጠፍቶኛል፡፡ ለምንም ወደእዛ እንደወሰደኝ አላውቅም፡፡ ሰው ባገኝ ብዬ ፔንጤ ጋር እሄድ ነበር እና፡፡ መኪናዬንም ውስጥ ብዙ ከተቀመጥኩ በሁዋላ፤ እዛው እበራፉ ላይ አቁሜ ገባሁ፡፡ እንደምንም ህይወቴን ማትረፍ እፈልጋለሁ፡፡ ሕይወቴን ግን ለምን እንደፈለኩት አላውቅም ነበር፡፡ ምንአልባት የናፈኩዋቸውን የተለየሁዋቸውን ልጆች ላለማስቀየም ይሆናል፡፡ እራሴን ብገል የሚያዝኑ እነሱ ብቻ እንደሚሆኑ አውቃለሁ፡፡ እንጂ ሕይወቴ መሮኝ ነበር አንገፍግፎኝ ነበር፡፡ አዎ ለልጆቼ ስል፤ እድሜ ልካቸውን ይህንን ያንን አድርገን በነበር እናታችን እራሱዋን አትገልም ነበር እንዳይሉ፡፡ እራሳቸውን ጥፋተኛ እንዳያደርጉ እና የማንንም ግፍ ፤የገፋኝን እና ያሰቃዩኝን ሀጢይት ተሸካሚ እንዳይሆኑ፡፡ ልክ ወደቤተክርስቲያኑ ስገባ፤ በራፍ ላይ የሚለምነው ሁሉ ተኮልኩሎአል፡፡ ኦርቶዶክሱም፤ ግማሹ ፍራንክ ግማሹ ዳቦ በመደዳው የተኮለኮሉትን ያድላል፡፡ አዎ የ አመቱ መድሃኒአለም ነበር ለካ ፡፡ ሰውም ነጫጭ ለብሶአል፡፡ ኮለል እያለ ወደደብሩ ይጠጋል፡፡ እኔም ግን ወደዛ አልሄድኩም፤ እግቢው ውስጥ ገባ ብዬ አንዲት ዳገት ላይ ዲንጋ ተደግፊ ቁጭ አልኩ፡፡ ጸሎትም የለኝም አደራም የለኝ፡፡ ግን አንድ ልቤን የሰበረው ነገር፤ ነበር፡፡ ሰው ናፍቆኝ አገር ናፍቆኝ መጥቼ ሰው ሳላገኝ ሰው ሳልተዋወቅ፤ ሰው ፈልጌ በሰው ተሰቃይቼ፤ ደሴን ለቅቄ መኮብለሌ ህዝቡ ሳያውቅ መለየቴ ነበር፡፡ እንባዬ እንደጎርፍ ይጎርፍ ነበር፡፡ የናፍኩዋት ኢትዮጲያ ለካስ እሱዋ አልናፈቀችኝም ፡፡ አንድ የሚያሳድደኝንም ፖሊስ በሩቅ አየሁት ልቤ በሲቃ ተሞላ በእልክ መታ፡፡ አይኔን ብዥ አለብኝ፡፡ አዲስ የሸመትኩት የፍርሃት እና የእልክ በሽታ፡፡
             ወዲያውም ከእኔ ጀርባ ኮረብታው ላይ አንድ ወጣት አስራ አምስት አመት በታች የሆነ፡፡ ከወገቡ በላይ እራቁቱን ነው፡፡ ሀፍረተስጋው ብቻ ቆዳ መሰል የተቀዳደደች ልብስ ተሸፍኖአል፡፡ ብዙ ነገሮች በአንገቱ ላይ አንጠልጥሎአል፡፡ ወዮልሽ ኢትዮጲያ፡፡ ወዮልሽ ደሴ የሚለው ድምጽ ነው በጀርባዬ ሰው መቆሙን ያየሁት፡፡ እኔም ከተቀመጥኩበት አልተነሳሁም፡፡ መድሃኒአለም ተመለሱ ይላል ሲል፡፡ የመድሃኒአለምን ቃል ስሰማ ልቤ ወከክ ይላል፡፡ የአይኔም ብዥታ ግፍፍ አለ፡፡ አንድ አንድ እያለ ሰውም ግጥም ማለት ጀመረ፡፡ እኔም ከዛ ውስጥ ወጣሁእና ወደመኪናዬ ላመራ ስል ድምጹን ከፍ እያደረገ መስበክ ጀመረ፡፡ ፌቴንም ዘወር አደረኩ፡፡ ወዩላችሁ እናንተ  መልካሙን የምትቀጥፉ፤ መልካሙን የምታባርሩ የሚለው ድምጽ በጆሮዬ አስተጋባ፡፡ ወዮላችሁ እነሱስ ምንም አይሆኑም እናንተ ግን ወዮላችሁ እያለ ቀጠለ፡፡ ከዛም መኪናዬ ውስጥ ገባሁ፡፡ ካለምንም ልብስ እና ጉዋዝ፤ የምሰናበተውም አልነበረኝም እና፤ ወደቤቴ አልተመለስኩም፡፡ፊቴንም ወደሁዋላ ዙሬ ለማየት አልደፈርኩም፡፡ እንባዬ በአይኔ እየተሞላ በምሃረቤ እየተረኩ  400 ኪሎሜትር ሀ ብዬ ከመድሃኒአለም ጀምሬ ወደ አዲስ አበባ ሸመጠጥኩ፡፡ ወደሁዋልም እንዳልዞር አንገቴ የደረቀ መሰለኝ፡፡ የመኪናውን ቴፔን ከፍ በማድረግ፤ የኦርቶዶክሱን ዘለሰኛ እና ደግሞም የፔንጤውን ሃያል ነው እግዚአብሄር የሚለውን እና ክብር ይገባሃል የሚለውን እየዘመርኩ አዲስ አበባ ገባሁ፡፡ የምሄድበትንም አላወኩት፡፡ የማርፍበትንም አላውቅም ነበር፡፡ያለፕላኑ የምሬት የፍርጠጣ ጉዞ፡፡
           መኪና ልንዳ እንጃ ሁሉም ግራ የገባ ነበር፡፡ ኪሴም ባዶ ሆኖአል፡፡ አላሰራኝ ብለው ነበር እና፤ አትራፊም አልሆንኩም፡፡ የሰራሁት ነገር ሁሉ ገደል ገብቶአል፡፡ ያለምኩት ሁሉ ቅዠት ሆኖአል፡፡ በፈረንጅ ጉዋደኞቼ በኩል ወደተዋወኩባት አንዲት ወዳጄ ቤት አመራሁ፡፡  ባለምርጡ ሬስቶራንት ባለቤት፡፡ ደፋ ቀና ብላ በስራ የተወጠረች፡፡ ወደዛም አመራሁ፡፡ ትዝ ያለኝ የደሴው የባህታዊው ምልእክት ነበር፤“ መልካምን የምታሰድዱ ፣ እናንተ ወዮላችሁ፣ እነሱ ግን ምንም አይሆኑ“ የሚለው ቃል ነበር፡፡ መልካም ነኝ ማለቴ ሳይሆን፤ እኔ ግን ማንንም አላሳደድኩም፤ አላሰቃየሁም እና፤ ቃላቱ ተስፋ ሆነኝ፡፡ እሱዋም በታላቅ ፈገግታ ተቀበለችኝ፡፡ ምግቡንም በጠረንጴዛው ሞላችው፡፡ እኔ ግን ሳላስበው እንባዬንም አፈሰስኩት፡፡ መንገዱ ያደከመኝ መስሎዋት ነበር እና፤ እንባው ግን እረበሻት፡፡ እሱዋም ምን ሆንሽ ምን ተበደልሽ ብላ አላጨናነቀችኝም፡፡ እንባዋ ግን አብሮ ፈሰሰ፡፡ ባይተዋር እንደተደረኩ ሳይገባት አልቀረም፡፡ እንዲህም አለችኝ፡፡ „አይዞሽ፡፡ ሁሉም ያለ ነው፡፡ መከራም ያለ ነው፡፡ ያልፋል፡፡ አሁን አዲስ ሀ ብለሽ ጀምሪ ፡፡ መኖር ስላለብሽ ለመኖር የሚረዳሽን አይምሮ አታበላሺ፡፡ ሻወር ውሰጂ፤ ከተማም ሄደን ልብስ እንግዛ፡፡ ልብስሽንም ቀይሪው፡፡ ጸጉርሽንም ነይ ተሰሪ፡፡ እዚህ እነዛ ያሰቃዩሽ ሰዎች የሉም፡፡ 400 ኪሎ ሜትር እርቀሻል፡፡“  እኔም ያለችኝን ምክር አደረኩ፡፡
            መኪናዬን መሸጥ ነበረብኝ፡፡ እና ጉዋደኛዬ እባክሽ አንቺ አስቀሪው አልኩዋት፡፡ እሱዋም ረጋ ባለ አነጋገር እንዲህ ስትል መለሰችልኝ፡፡  „ጉዋደኛዬ አንቺ እኮ ከስረሽ ነው የምትሸጭው እንጂ ሌላ መኪና ቀይረሽ አይደለም፡፡ ስለዚህ እኔ በጉዋደኛዬ ክስረት አላተርፍም፡፡ ቀን ያልፋል፡፡ ቢኖረኝ በሰጠሁሽ ካልሆነም ባበደርኩሽ ነበር „፡፡እሱዋ ስራዋ አድጎ ሰራተኛውም በዝቶ ለስራም ሁለተኛ መኪና ያስፈልጋት ነበርእና፡፡ በኪሳራ እንደምሸጠው ስላወቀች፤ እሱዋ ግን በጭራሽ አልገዛውም አለች፡፡ እባክሽ አስቀሪው አንቺ ጋር ይግባ፤ ብየም ለመንኩዋት፡፡ ባዩሽዬ ፤ብትጥይውም ጣይው እንጂ፤ እኔ ግን አልገዛውም፡፡ እኛ እኮ  የምንቀጥል ጉዋደኛሞች ነን፡፡ በተገናኘን ቁጥር ይህንን መኪና እያየሽ ክፉ ግዜሽን በእኔ ቤት እንድታስታውሽው አልፈልግም ብላ ዘጋች፡፡ የሚገርመው ይህቺ መልካም እና አስተዋይ ህይወቴንም የታደገች እና ያጽናናች ሴት ከትግራይ ቤተሰቦች የተወለደች ትገሬ ነበረች፡፡ ፍቅር ከእግዚአብሄር ሲሆን ምላሹም ማዳን፤ መረዳት እና እንባን መጥረግ ይሆናል፡፡ ግን ፍቅር ከሰይጣን ሲሆን ከጥቅም ጋር ይያያዛል፡፡ አመሰግናለሁ፡፡ ቀን ቢገጥመኝ በአንድ ሚዲያ አግንቻት አመሰግናለሁ ብላት ለብዙ ሚሊዮን ህዝብ ትምህርት በሆነ ነበር፡፡ ግና ምንአልባት አጋጣሚው ላይመቻችልኝ ይችላል፡፡ አላውቅም ነገ ምን እንደሚያመጣ፡፡ ደግመንም ካልተገኛኘን፡ እግዚአብሄር ዘመኑዋን ሁሉ ይባርክ፡፡ እሱዋ በዛን ሰአት ባትገኝ ምን እንደሚገጥመኝ ለእናንተ ልተወው፡፡ ሰላማችሁ ይብዛ፡፡  
ባዩሽ

Donnerstag, 4. Juni 2015

ሴቶች???? „ መጣፈጥህ ቀርቶ፤ ግምህ በለቀቀኝ“



           በውነቱ የሴቶችን ችግር ተቃዋሚም ሆነ ገዢው ፓርቲ መፍተሄ ሊሰጠው አይችልም፡፡ ምክናያቱም ህግን ማስፈጸም የሚችለው አካል ሁሉ በቂ የሆነ በሴቶች ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን መጥፎ እንደሆኑ እና እንዴት መረዳት እንዳለባቸው፤ ጉዳቱስ ምን እንደሚመስል ምንም አይነት ትምህርትም ሆነ ንቃተህሊና የሰጣቸው ዮፖለቲካ አካል ስለሌለለ ነው፡፡ በአጠቃላየይ የሴቶች ጉዳይ በኢትዮጲያ ግንዛቤን የሚያስጨብጥ ስራ አልተሰራም፡፡ ያሰበውም የለም፡፡ አዎ የሴቶች እኩልነት ተብሎ በሁልም ይነገራል፡፡ ግን „ መጣፈጥሽ ቀርቶ ግምሽ በለለቀኝ“  ሆነእና ነገሩ፤ ከአፍ ወሬ ያላለፈ እና ዝም ብሎ የውጩችን ዲሞክራቲክ ነን ከሚለው ፕሮፖጋንዳ የተለዬ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ የሚገርመው ሕግ አውጪዎችም ሆነ ሕጉን አስከባሪዎቹ የሴት ችግር ምንነቱንም የሚያውቁት አይደለም፡፡ የሴት የመጀመሪየያው ቀዳሚው ነጻነቱዋ  ባሉዋን መፍታት እና ማግባት ላይ የተወሰነ እኩይ ምግባር አይደለም፡፡ የሴቶች ትግል ትዳርን የሚከለክል አይደለም፡፡ ይህ ውሸት የሆነ እይታ፤ ያልነቃ ህሊና የሚያስበው ነው፡፡  በውንድ ግንኙነት ብቻ የተመሰረተ ችግር አይደለም፡፡ ብዙ የታዘብኩት ፤ የሴቶች ትግል ማለት ባልእና ሚስትን በማፋታት የሚያበቃ አልያም የተወሰነ ደግሞም ሴቱዋን ሳታገባ የሚያስቀር አይነት እኩልነት አይደለም፡፡ ይህ ከሆነ እኩልነት ሳይሆን ጎዶሎነት ነው፡፡ የሴቶች ትግል ማለት፤ የመጀመሪያው ሴትንም በእኩልነት ከኢኮኖሚ ጥገኝነት የሚያወጣት ዋንኛውን ትግል መስፈረት የሚመለከት ትግል ነው፡፡ በኢኮኖሚ እራሱዋን ያልቻለችን ሴት ከወንድ ለመለየት መጣር ይህ እራሱ ሴቱዋን ከቤት ወደልመና የሚከት አልያም ወደሴት አዳሪነት የሚገፋፋ ነው፡፡
                በዚህም የተነሳ ሴት ለምታደርገው ማንኛውም የኢኮኖሚ ተጽእኖ ማንም የሚረዳት የሚተባበራት አካል የለም፡፡ እንዳውም ሴት  እንድትሰራ ድሮም አልተከለከለችም፡፡ግን እንድትቀጥልበት እና እንድታድግ የሚያደርጋትን ቀውስ ሊነሳላት ቀርቶ ጭራሽ የበለጠ በየአቅጣጫው እንድትበዘበዝ እና ሞራልዋ እንዲነካ የሆነበት ሁኔታ ነው የሚታየው፡፡ ለምሳሌ አቶ መለስ በስልጣን በነበሩበት ግዜ እንኩዋን የታየው ሁኔታ አሁን ጭራሽ ደዝባው እንዲጠፋ ተደርጎአል፡፡ ይህ የጸጥታ አስከባሪ እና ደግሞም የመንግስት ህግ አስፈጻሚዎች እራሳቸው ለሴት እኩልነት ያላቸው ክብር ዝቅ ያለ በመሆኑ እና በነጻነቱዋም ስለማያምኑበት፤ ለሚደርስባት ተጽእኖ ሁሉም ምንም አጋዥነት የላቸውም፡፡ ሴቶች ነጻ ወጥተዋል ብለው የሚያምኑት፤በእራሳቸው አካባቢ ያሰለፉዋቸውን ደመወዝተኞች ከቁጥር በማብዛት ነው፡፡ እነዚህ ሴቶች ደግሞ ከ80% በላይ ያለውን በኢኮኖሚ እራሱን ለማስቻል ያልቻለውን ሴቶች በጭራሽ አይወክልም፡፡
              በአለም ዙሪያ የቢሮ ሴቶችም ቢሆን ያለባቸው ጫና በእውቀት ሳይሆን ውድድሩ በዘመድ አልያም ሴቱዋ በምታሳየው እራስን አሸብርቆ በማቅረብ መሆኑ ይነገራል፡፡ ይህ ደግሞ የወንድ ወንዶች አለም፤ እንኩዋን ሴትዋን ወንዱንም ያርበተበተ ያስጨነቀ በመሆኑ፤ ይህንን  ስራአት ለመቁዋቁዋም አንዳንድ ሴቶች ከመጠን ያለፈ እራሳቸውን በሜክአፕ በውድ ልብስ እና ጌጣጌጥ በማሸብረቅ፤ ከሌላዋ ሴት በልጠው አለቆቻቸውን ለመማረክ ይጥራሉ፡፡ ትንሹዋን የተፈቀደችውን ቦታ ለማሸነፍ ማለት ነው፡፡ ይህ ዘወትር   እውቀት ያላቸው እና በእውቀታቸው ማደግ ያልቻሉ ሴቶች  የሚያሰሙት  ምሬት ነው፡፡ ስራቸውን ከማሳየት ይልቅ መልካቸውን እና አለባበሳቸውን የሚያዩ ብዙም ወንድ አለቆች እንዳሉ ይነገራል፡፡ እድገት በብልህነት እና በማወቅ ሳይሆን በመልክ መሆኑ ብዙ ግዜ የሴቶችን እድገት እንደሚገደብ ይነገራል፡፡ ለውድድሩም የገባችው ሴት፤ ደመወዝዋ የሚውለው ለዚሁ ጌጣ ጌጥ በመሆኑ፤ ትዳር ስትይዝ ለትዳሩዋ እና ለቤተሰብዋ አጋዥ የማትሆንበት ብዙ የኢኮኖሚ ቀውስ ይፈጠራል፡፡ እንዳውም አንዳንድ ባሎች የእሱዋ ደመወዝ ተጨማሪ ወጪ ነው ያመጣብኝ፤ እቤት ብትውል ይሻል ነበር የሚሉም እና ምሬት የሚያሳዩም አልጠፉም፡፡ ሴቶችን ወንዶች ወደአድባባይ ወደትምህርት ቤት እና ወደማወቅ የሚያደርጉትን ግፊት እና የአደባባይ አመኔታ ይቀንሳል፡፡ ምክናያቱም በዚህ የአንድ ሱሪ ጫማ ወይም የአንድ ቀሚስ ዋጋ ከአንድ ኩንታል ጤፍ በሚበልጥበት የኩዋሊቲ ውድድር፤ ሁኔታው የባልንም ባጀት አይነካም ማለት ዘበት ነው፡፡ ለውድድሩ የሚፍጨረጨሩትን ሴቶች ሁኔታ ለመጥቀስ ነው፡፡ አይ እውቀቴ ብቻ ነው የሚበቃኝ ያለች ሴት ስራ ቢኖራትም ምንአልባትም በእውቀት ከእሱዋ በታች ለሆኑ ሴቶች ታዛዥ መሆኑዋ የማይቀር ሀቅ ነው፡፡ እሱዋ በምትሰራው ሌላው የሚያድግበት ሁኔታም ይኖራል፡፡ ታዲያ የጥቂት ሴቶች እድገት ብዙሃኑን የሚወክል ከቶም ሊሆን አልቻለም፡፡ፖለቲካው የሚያፈራው ዘወትር በእራሳቸው የተጠመዱ ወንዶች እና ሴቶችን መሆኑ ይታያል፡፤ ለሌላውም አይምሮ እድገት አይተርፍም፡፡ ዘወትር ሴቶች በጌጣ ጌጥ አለም እንዲያምኑ ማድረግ፤ የተማሩትንም ሴቶች ቢሆን ለስደት የሚጋብዝ ነው፡፡ እውጭ አገር ብትመጣ በተማረችው ስራም ባታገኝም ለቁሳቁሱ መግዣ የእጥፍ እጥፍም ታተርፋለች፡፡ በዚህም የተነሳ ስደቱ እንዳው ስራ ያጣውን ብቻ ሳይሆን፤ በየመስሪያ ቤቱ የሚደረገው የንዋይ ውድድር እድገቱዋን እንደሚቀንሰው ስለምታውቅ፤ ስደትን ማሰቡዋ የማየቀር ነው፡፡
                 የሴቶች ችግር መፍተሄ የሚያገኘው፤ በሚንስተር ጽ/ቤት የተቀመጡ ፖለቲከኞች ፍላጎት ወይም እነሱ ባዘዙት የሚፈጸም ሳይሆን፤ በዚህ ነገር ላይ በመንግስት ተቁዋም ውስጥ ያሉ ወንዶች ፤በሴቶች ጉዳይ ላይ በቂ ግንዛቤ ሲያካብቱ እና ሲማሩ ብቻ ነው፡፡  ስራ አስፈጻሚዎች አልያም ሲቪል ሰርቫንቱ፤   ህብረተሱቡ ውስጥ ሰርጾ የሚገባ የለውጥ ድማም ማሳየት ይጠበቅባቸው ነበር፡፡ የፈለገው የሴቶች ህግ ቢደነገግ፤ ባልነቃ ህብረተሰብ መካከል የህልም እሩጫ ይሆናል፡፡ ይህም ያመጣው ቀውስ እራሳቸው በሴቶች ጉዳይ ላይ በቂ ግንዛቤ የለላቸው ፖለቲከኞች በስልጣን ስለሚቀመጡ ነው፡፡ በዚህም የተነሳ አነሰም አደገም ማንኛውም ሴት በኢኮኖሚ እራሱዋን ለመርዳት የምታደርገው ጥረት ምንም አይነት እርምጃ ሊያሳይ አልቻለም፡፡ ጭራሽ አቶመለስ ከሞቱ በሁዋላ በአቶ ሀይለማርያም ግዜ ያለው ሁኔታ፤ የፈጠረው ክስተት፤ ልክ ሴትን እንደፈለክ አድርግ ተብሎ የተላለፈ ሰርኩላር  ያለ እስኪመስል ድረስ፤ በህብረተሰቡ መካከል የሚያለቅሱ ሴቶች እጅግ በዝተው ይታዩ ነበር፡፡ ለምሳሌ አንዲት በቡና ቤት ውስጥ የምትሰራ ወጣት፤ አንዱ ከከፈላት በሁዋላ ሌላው ጉዋደኛውም አብሮ ሊጠቀምባት የተነሳው ጋጥ ወጥነት፤ አቶ መለስ ከሞቱ በሁወላ በድምቀት ሰብሮ የወጣ አይን አውጣ የሆነ ልቅ ባህል ይዞ የወጣ ነው፡፡ ብዙ ሴቶችም እራሳቸውን ለማቁዋቁዋም ያደረጉት ጥረት አልሳካ ያለበት እና ተስፋቸው የተሙዋጠጠበት እና ስራቸውን እንዲተው የተደረጉትም አሁን አቶ ሀይለማርያም በስልጣን ከሆኑ በሁዋላ ነው፡፡ የከተማው ፖሊሶች የሴትን ጉዳይ በንቀት እና በማሾፍ የተመለከቱትም የበለጠውን ግዜ የያዘው ባለፉት ሶስት አመቶች ነው፡፡ የሴት ሞራል በእጅጉ አዘቅት ውስጥ የገባው ዛሬ አቶ ሀይለማርያም ጠቅላይ ሚኒስተር ከሆኑ በሁዋላ ነው፡፡ በአረብ አገር ሴቶች በእጅጉ መንገላታት እየደመቀ የመጣውም፤ እና ይፋ የወጣውም፤ አቶ ሀይለማርያም ስልጣን ላይ ከወጡ በሁዋላ ነው፡፡ አንዲት ልጅ በ5 ወንዶች አዲስ አበባ ላይ ለአምስት ሬፕ ተደርጋ የሞተችው በአቶ ሀይለማርያም ግዜ ነው፡፡ ይህ ሁሉ ልቅነት የመጣው መንግስት ስለፈለገው ሳይሆን በሴቶች ላይ ለሚደረገው ተጽእኖ የተሰጠው ቀዳሚ ስፍራ  እንደገና ደዝባው እየጠፋ እና እየተረሳ በመሄዱ ነው፡፡ ከዛም በላይ መንግስት የሚያደርገው እርብርብ እራሱ ያመነበት ሽብር በሚለው ነገር ላይ እንጂ፤ ባላመነበት ግን ባለው የሴቶች ጉዳይ ላይ አይደለም፡፡ ይህም እራሴን ስለሚመለከተኝ ነው፡፡ ሰው እራሱን ነጻ ሳያወጣ ሌላውን ነጻነት ማውጣት አይችልም፡፡
ብዙ አደባባይ የማያውቃቸውም ተግባሮች ተፈጽመው፤ ሚዲያ ባለማግኘት አልያም በባህል ተጽእኖ የተነሳ ተድበስብሶ ሊሆን እንደሚችል ጥርጥር የለውም፡፡ ይሁን እና ግን የሴቶች ጉዳይ ህግ በመደንገግ ብቻ የሚያበቃ አይደለም ብዙ ፍቅር እና መረዳትን የሚጠይቅ ተግባር በመሆኑ፤ የሰው አስተሳሰቡ ካልተቀየረ የህግ የበላይነት መስመር ይይዛል የሚለው አመለካከቴ ለጊዜው በአለት ላይ ቤት እንደመስራት ሆኖ አይቸዋለሁ፡፡ እኔ እራሴ እዚህ የምጮህ፤ መስራት እና መኖር የምችልበት ሁኔታ በመናቁ እና በመዘንጋቱ፤ ጥቃቱም የሚያስቆመው የህግ የበላይነት ተፈጻሚ ሆኖ ለማየት ባለመቻሌ ነው፡፡ እኔ ኢህአዴግ ስራ ይሰጠኛል፤ ወይም ተቀዋሚ ሲመጣም ስራ ይሰጠኛል የሚል ህልም ሰንቄ አልተነሳሁም፡፡ ምንአልባት ግን ለዘመናት የተጨቆንኩበትን የታሰርኩበትን ነጻነት በጸጥታው በኩል ሊተባበሩኝ ጥቃትን ሊከላከሉልኝ ይችላሉ የሚል የህግ ተፈጻሚነትን ፣ተስፋ እና እምነት ይዠ ካልሆነ በቀር፡፡ እሱም አፈርድሜ በልቶአል፡፡ ህግ አስከባሪውም እራሱ አጥቂ ሆኖ በማየቴ እጅግ አዝኛለሁ፡፡ በቃ ሴቶች ስራ ለመፍጠር የሚያበረታታ አካልም ሆነ የህግ የበላይነት በምድሪቱዋ ኢትዮጲያ ላይ አይታይም፡፡ እንኩዋን ሕጉ ለእኔ ሊወክልኝ ሊሙዋገትልኝ ቀርቶ እራሱ ህጉ የሚሞግተኝ ሳላጠፋ የሚቀጣኝ እንዲሆን የህግ አስከባሪዎች እና አስፈጻሚዎች አድርገውታል፡፡   
         ያም ያም የሚጎስማት ሴት ላይ ጭራሽ እራሳቸውም ፖለቲከኞች ህግ አስፈጻሚዎች እና ጸጥታ አስከባሪዎች ለሴት ያላቸው ግንዛቤ ዜሮ ነው፡፤ ተቃዋሚ የተሻለ ነው ለማለትም ገና አልደረስኩም፡፡ ሁሉም የሚታፈርበት ግን ልትዘነጉት የማትችሉት ጉዳይ መሆኑን ልብ እንድትሉ እና ንቃተህሊናችሁን እንድታዳብሩ እጠብቃለሁ፡፡ ማንም የፖለቲካ ፓርቲ ለሴት ስራ መፍጠር የሚችልበት ሁኔታ በለለበት ኢትዮጲያ፤ ሰርታ እንዳትበላ እየተደረገ ነው፡፡ ይህም የህግ እና የሚገባው የህግ ትብብር፤ በንግድ ሚኒስተር፣ በአገርውስጥ ገቢ፣ በአስተዳደር፣ እና በጸጥታ አስከባሪዎች ብሎም ማንኛውም ተቁዋም፤ ምንም አይነት የመረዳት እና የመርዳት ንቅናቄ የለውም፡፡ ለዘመናት በጥገኝነት በድርብ ተጽእኖ ታስራ የምትኖር ሴት፤ ከጉዋዳ ወጥታ ወደአደባባይ እራሱዋን ለመርዳት የምታደርገው ጥረት ጭራሽ አስደንጋጭ፣ አሸማቃቂ፣ አሳፋሪ እና አስበርጋጊ ሆኖአል፡፡
            ግን ሰርቼ ደግሞ ዳቦዬን ለመብላት ፤አስፈላጊውን ጸጥታ ለማግኘት እና በሴትነቴ እንድደገፍ፤ ለማድረግ ደግሞ ፖለቲከኞቻችን ዘመናዊ ፓለቲካን ማራመድ ግድ ባላቸው ነበር፡፡ ግን አሁንም ቢሆን አስተዳደሩ ከወንዶች አለም፤ ከአባጋሮች አስተሳሰብ የወጣ መስፈርት የወጣ ነገር የለውም፡፡ ኑሮ በጉልበት አድርገውታል፡፡ ስለዚህ ለፖለቲከኞችም እራሱ በሴቶች ጉዳይ ንቃተ ህሊናቸው ዜሮ በዜሮ ነው ብል ላፍርበት አይገባኝም፤ በአይኔ የማየው በእጄ የዳሰስኩት፤ በአይምሮዬ የማይጠፋ ጥፋቶችን በመኖር ስቃዩን አይቻለሁ እና፡፡ በዚህ በኩል ሁለቱም ተቃዋሚዎችም ገዢውም ፓርቲም እኩል እንደሚሆኑ አልጠራጠርም፡፡ ምክናያቱም የሴቶች ትግል ፍቅርን እና መረዳት ይላል እና፡፡ እነዚህ ተረዳድተው ተራርቀው የማይሰሩ ፖለቲከኞች ለሴቶች ለውጥ ያመጣሉ ብዬ መገመት አልችልም፡፡ ምክናያቱም የሴቶችን ጥቃት የሚያመጣው የሁለቱ ፍጥጫ ወደሃይል የተለወጠ በመሆኑ፤ በህብረተሰቡ መካከልም ለሴት ሀይለኛ ህግ አላባ ይፈጥራል እና፡፡
ሴቶች በብዛት የሚጠቁት ፖለቲከኞች በጋራ የማይሰሩበት፤ የሚፈራሩበት አገር ላይ ነው፡፡ ሁከት ለሴቶች እና ለህጻናቶች ጥቃት ከፍተኛ የሆነ አስተዋጽኦ የሚያደርግ ነው፡፡የሁለቱ መጠባበቅ በህብረተሰብ ውስጥ ደካማ ሆነው የሚገኙትን የሚያበረታታ ነገር አይፈጥርም፡፡  እነሱንስ ማን ይጠብቃቸው? እኔ የምታገለው የእራሴም መብት ስለተነካ ነው፡፡ የተነካች እና እኔም እነካለሁ ያለች ሴት ለእራሱዋ ስትል ለመብቱዋ ትነሳ፡፤ ትንሳ ስል ዘነዘና አንሺ ማለቴ አይደለም፡፡ ግን እራሱ እንዴትም እንደተጨቆንሽ ለማገናዘብ አይንሽን እና አይምሮሽን ክፈቼ፤፤ ሴት ሆይ ሰው እንጂ እንሰሳ አይደለሽም፡፡ እናት፣ እህት፣ ሚስት፣ እና ልጅ ነሽ፡፡ አንቺ የአገር ምሶሶ ነሽ አንቺ ፈረሽ ማለት አገር የለም ማለት ነው፡፡ቤተሰብም የለም ማለት ነው፡፡ ይህን ወንዶች አያውቁትም፡፡ ምክናያቱም ወንዶችን እንደማትወዳደሪ አድርገውታል እና፡፡ ሴትን ያልባረከ አይባረክም፡፡ እናት ሆነሽ አምጠሻል ወልደሻል እና፡፡ ትውልድ ሁሉም ሊያመሰግንሽ ይገባል፡፡
ባዩሽ